ታምሩ ወንድማገኘሁ፣ መስፍን ታፈሰ (MTA)፣ መቅደስ እና ሃና ሙሉጌታ የተባሉ አራት ታዋቂ የህግ ድርጅቶች በመዋሃድ «ታዛ ሌጋል» የተሰኘ ግዙፍ የህግ ተቋም በይፋ መሥረታቸውን ሰኔ 18 ቀን 2018 ዓ.ም በንግድ ባንክ ዋና መሥሪያ ቤት አስታውቀዋል።
ይህ ውህደት የሀገሪቱን እያደገ የመጣውን የኮርፖሬት፣ የኢንቨስትመንት እና የፋይናንስ ዘርፍ ፍላጎት ለማሟላት ያለመ ነው።
ከ100 ዓመታት በላይ ድምር ልምድ፣ 7 አጋሮችና 20 ባለሙያዎችን የያዘው ታዛ ሌጋል፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሆነ የህግ ምክርና ክርክር አገልግሎት በአንድ ማዕከል ያቀርባል።
የተቋሙ ማኔጂንግ ፓርትነር አቶ መስፍን ታፈሰ እንደገለጹት፣ ውህደቱ ከግለሰብ ባለሙያዎች ጥገኝነት ወጥቶ ዘላቂ ተቋም ለመገንባትና ቀጣዩን የህግ ባለሙያዎች ትውልድ ለማፍራት ትልቅ ዕድል ይፈጥራል። ታዛ ሌጋል የአፍሪካ የህግ ትስስር (ALN) አባል በመሆንም ዓለም አቀፋዊ ተደራሽነቱን ያሰፋል።
