ቪኦኤ እንደዘገበው፤ ከ800 በላይ የህግ ባለሙያዎች፣ ምሁራንና የቀድሞ ዳኞች እንግሊዝ በእስራኤል መንግሥት ላይ ማዕቀብ እንድትጥል ጥሪ አቅርበዋል፡፡
የፍትህ አካላቱ ባለፈው ሰኞ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኬይር ስታርመር በላኩት ግልጽ ደብዳቤ፣ የእንግሊዝ መንግስት እስራኤል እየፈጸመች ያለውን “ከባድ የአለም አቀፍ ህግ ጥሰቶች” ለማስቆም ተጨባጭ እርምጃ መውሰድ አለበት ብለዋል፡፡
“በጋዛ የዘር ማጥፋት ወንጀል እየተፈፀመ ነው ወይም ቢያንስ የዘር ማጥፋት ከፍተኛ አደጋ አለ” ብለዋል፤ በደብዳቤያቸው፡፡
በጋዛ የፍልስጤም ህዝብ ላይ የሚደርሰውን ውድመት ለመከላከል አስቸኳይና ወሳኝ እርምጃ እንደሚያስፈልግ የሚጠቁመው ደብዳቤው፤ ስታርመር አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጡ ማሳሰቡን ዘገባው አመልክቷል፡፡
የእስራኤል የገንዘብ ሚኒስትር ቤዛሌል ስሞትሪች በቅርቡ የሰጧቸውን አስተያየቶች በመጥቀስም፣ እስራኤል “የጋዛ ሰርጥ ግዛትን በሙሉ ለመቆጣጠርና ለማጽዳት እንዲሁም ሃማስ እስኪጠፋ ድረስ ለመቆየት” ያላትን ፍላጎት ጠቁሟል፡፡
በቀጠለው የእስራኤል ጥቃት በጋዛ ሰርጥ በሚገኙ ሆስፒታሎች ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ ቢያንስ 79 ሰዎች ሲገደሉ፣ 163 ያህሉ ደግሞ ቆስለዋል። አሃዙ ጦርነቱ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ የተገደሉትን ሰዎች ቁጥር ወደ 54ሺ 56 ያደረሰው ሲሆን፤ 123ሺ 1መቶ 29 ሰዎች ቆስለዋል።
