የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ የጊዜ ቀጠሮ ችሎት ከገቢ አሰባሰብ ጋር በተያያዘ በከባድ የሙስና ወንጀል በተጠረጠሩ 41 የገቢዎች ሚኒስቴር ከፍተኛ ኃላፊዎች፣ ባለሙያዎች እና ተባባሪ ግለሰቦች ላይ የ14 ቀናት የምርመራ ጊዜ ፈቀደ።
በዛሬው ዕለት ችሎቱ የተጠርጣሪዎችን ማንነት በማረጋገጥ የግራ ቀኙን ክርክር አዳምጧል።
ፖሊስ ለችሎቱ በሰጠው ማስረገጫ፣ የተፈጸመው ወንጀል በመደራጀት የተካሄደ የኢኮኖሚ አሻጥር በመሆኑ ሰፊ እና ውስብስብ ነው ብሏል።
በመሆኑም የደረሰውን የጉዳት መጠን በኦዲት ለማረጋገጥ፣ በቂ ማጣሪያ ለማድረግ እና የምርመራ መዝገቡን አደራጅቶ ለማቅረብ የ14 ቀናት ተጨማሪ ጊዜ እንዲሰጠው ጠይቋል።
ፖሊስ አክሎም የጉዳት መጠኑን በቀጣይ ቀጠሮ ይፋ እንደሚያደርግ በመግለጽ፣ ተጠርጣሪዎቹ በዋስ ቢለቀቁ ምስክሮችን ሊያባብሉ እና ሰነዶችን ሊያጠፉ ይችላሉ በሚል የዋስትና ጥያቄያቸውን ተቃውሟል።
በሌላ በኩል የተጠርጣሪ ጠበቆች ፖሊስ ያቀረበው ጥርጣሬ በቂ እንዳልሆነና በጥቅሉ የቀረበ ነው ሲሉ ተከራክረዋል። አቃቤ ህግ እና መርማሪ ፖሊስ ጊዜ ለመግዛት ሲሉ የቀረቡ ምክንያት እንደሆኑ በመጥቀስ፣ የተጠርጣሪዎችን የጤና ሁኔታ እና የማቆያ ቦታ ጥበት ታሳቢ በማድረግ በዋስ ወጥተው በውጭ ሆነው እንዲከራከሩ ጠይቀዋል።
የግራ ቀኙን ክርክር ያዳመጠው እና የፖሊስን የምርመራ መዝገብ የተመለከተው ችሎቱ፣ በቂ ጥርጣሬ መኖሩን በመረዳቱ እንዲሁም የጉዳት መጠኑን እና የግለሰቦችን ተሳትፎ ለይቶ ማቅረብ አስፈላጊ መሆኑን በመቀበል የምርመራ ጊዜውን ፈቅዷል።
በዚህም መሠረት ጉዳያቸው መታየት ከጀመረበት ከሐምሌ 30 እና ነሐሴ 1 ቀን ጀምሮ የሚታሰብ የ14 ቀናት የምርመራ ጊዜ የተፈቀደ ሲሆን፣ የፖሊስ ማጣሪያ ውጤትን ለመመልከት ለነሐሴ 14 እና 15 ቀን 2018 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል። በተጨማሪም በተጠርጣሪዎች የጤና ሁኔታ እና አያያዝ ላይ አስፈላጊው እንክብካቤ እንዲደረግ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ አስተላልፏል።
