የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ በ2018 የትምህርት ዘመን ለተማሪዎች መማሪያ የሚውሉ የመማሪያ ደብተሮች ስርጭት እያከናወነ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ምክትል ቢሮ ሃላፊ አቶ ሳምሶን መለሰ ለብስራት ሬዲዮ እንደተናገሩት በ90 ቀናት ውስጥ ታቅደው እየተከናወኑ ከሚገኙ ተግባራት መካከል ለ2018 የትምህርት ዘመን አገልግሎት የሚውሉ የተለያዩ የመማሪያና ማስተማሪያ ግብዓቶች ስርጭት አንድ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ሃላፊው አክለውም የመማሪያ ደብተሩ ስርጭት ቀደም ሲል ለክፍለ ከተማዎች 60 በመቶ መሰጠቱን ጠቅሰው ቀሪ 40 በመቶ መማሪያ ደብተሮች አሁን ላይ በመሰራጨት ላይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
አያይዘውም ከዚህ ቀደም ከደንብ ልብሶች ስርጭት ጋር ተያይዞ ይነሳ የነበረዉን በወቅቱ ይድረስልን ጥያቄ በ90 ቀናት እቅድ ውስጥ ተካቶ በመሰራቱ በ21 ጋርመንቶች የተመረቱ የደንብ ልብሶች ትምህርት ከመጀመሩ በፊት በየትምህርት ቤቶቹ በመሰራጨት ላይ መሆናቸዉን ተናግረዋል፡፡
በ2018 የትምህርት ዘመን የተማሪ ደንብ ልብስና የመማሪያ ደብተር ስርጭት በመከናወኑ ከዚህ በፊት ይነሱ የነበሩ ቅሬታዎችን የሚፈታ ይሆናል ተብሏል።
