የክልሉ ፕሬዚዳንት ተደርገው የተመረጡት ድብርጺዮን ገ/ ሚካዔል (ዶ/ር) ቃለ ማህላ መፈጸማቸውን ሕወሓት አሳውቀቋል፡፡
ድርጅቱ ከድብረጺዮን ገብረሚካዔል በተጨማሪ ወ/ሮ ኪሮስ ሓጎስን ዋና አፈ ጉባዔ እንዲሁም ወ/ሮ ምህረት በርሕን ምክትል አፈጉባዔ አድርጎ መምረጡን ይፋ አድርጓል፡፡
ለክልሉ ፕሬዚዳንት እና የምክር ቤት አፈ ጉባዔዎችን የመረጠው ምክር ቤት በክልሉ ደም አፋሳሹ ጦርነት እንዲካሄድ ምክንያት ነበር በተባለው የ2012 ምርጫ የተመረጠ መሆኑ ይታወቃል።
የሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ሚያዚያ 11 ቀን 2018 ባወጣው መግለጫ ሕወሓት በ2012 ዓ.ም ተካሂዶ በነበረው ምርጫ የተመረጠው የክልሉ ምክር ቤት ወደ ስራ እንዲመለስ መወሰኑ ይታወሳል፡፡
ሕወሓት ወደ ስራ እንዲመለስ የወሰነው ምክር ቤት በፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ወድቅ የተደረገ መሆኑ ይታወቃል፡፡
ውሳኔውን ተከትሎ በክልሉ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ድርጅቶች እና የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ክልሉን ዳግም ወደ አስከፊ እና ደም አፋሳሽ ጦርነት ሊከት ይችላል በሚል ስጋታቸውን ሲያነሱ ቆይተዋል።
ይህን ተከትሎም ድርጅቱ የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት ሌትና ጀነራል ታደሰ ወረደ ሰላማዊ የስልጣን ርክክብር እንደሚደረግም ማሳሰቡ ይታወሳል፡፡
ይሁንና የጊዜዊ አስተዳደሩ ፕሬዚዳንቱ ሌተና ጀነራል ታደሰ ወረደ የሕወሓት ውሳኔ በክልሉ የሰፈነውን አንጻራዊ ሰላም የሚያደፈርስ እና ለዳግም ጦርነት ምክንያት ሊሆን እንደሚችል ከቀናት በፊት አስጠንቅቀዋል፡፡
ሕወሓት በላያቸው ላይ አዲስ ፕሬዚዳንት አድርጎ የመረጠባቸው ሌትና ጀነራል ታደሰ ወረደ የመጀመሪያ ዙር የስልጣን ጊዜያቸው አብቅቶ ለተጨማሪ አንድ ዓመት ክልሉን እንዲመሩ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ የተሾሙት ከሳምንታት በፊት ነበር፡፡
የደብረጺዮን ገ/ሚካዔል ሹመት ተከትሎ እስካሁን ከጊዜያዊ አስተዳደሩም ሆነ ከፌዴራል መንግስት በኩል የተባለ ነገር የለም።
ሸገር 102.1
