በሀገር አቀፍ ደረጃ 102 የሚዲያ ተቋማትን በአባልነት የያዘው የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ምክር ቤት ከ የመንግስት የመገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን ጋር በፈጠረው አለመግባባት ዙሪያ በአስቸኳይ ለመወያየት ዝግጁ መሆኑን አስታውቋል።
ምክር ቤቱ “የመገናኛ ብዙሃን ባለሞያዎች ምዝገባና የብቃት እዉቅና ማረጋገጫ” ለመስጠት እየተንቀሳቀሰ ቢገኝም ባለስልጣኑ በትላንትናዉ ዕለት ይህን እንደማይቀበለው በይፋ በመግለጹ ምክር ቤቱ ቅር አሰኝቷል።
ምክር ቤቱ እንዳለዉ ባለስልጣኑ ያወጣው መግለጫ ሁለቱ ተቋማት ቀደም ሲል የተፈራረሙትን የመግባቢያ ሰነድ ያላከበረ ከመሆኑም በላይ ምንም አይነት ቅድመ ውይይት ሳይደረግበት ይፋ መደረጉን አስታውቋል።
ተቋሙ አክሎም ይህንን ስልጣን በአዋጅ የሚሰጠው የመንግስት መስሪያ ቤት እንደሆነ ይታወቃል፤ ምክር ቤቱ ግን ሚዲያው ራሱን በራሱ ለመቆጣጠር በሚል በፍቃደኝነት የተቋቋመ እና ከመንግስት ነፃ የሆነ ተቋም መሆኑን አስረድቷል።
በተጨማሪም ምክር ቤቱ ለአባላቱ መታወቂያ መስጠት ምን ችግር አለው ሲል በመጠየቅ የመገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን ያወጣው መግለጫ ጉዳዩን በግልፅ ካለመረዳት ወይም ካለማወቅ የተነሳ ሊሆን እንደሚችል ገልጿል።
ይህ እርምጃ በሀገሪቱ ውስጥ ያሉ ጋዜጠኞችን ቁጥር ለማረጋገጥም ጠቃሚ መሆኑን አጽንኦት ሰጥቷል።
በዚህ መሰረት ከባለስልጣኑ ጋር በጉዳዩ ዙሪያ በአስቸኳይ ለመወያየት ዝግጁ መሆኑን የገለጸ ሲሆን በዚህ ሳምንትም መፍትሄ ያገኛሉ ብሎ እንደሚጠብቅ አስታውቋል።
ምክር ቤቱ የሙያ ማንነት ምዝገባና እውቅና ማረጋገጫ ሐሳብ ወደ ሥራ ከመግባቱ በፊት ከባለሥልጣኑ ጋር ውይይትና በፊርማ ደረጃ ስምምነት ተፈፃሚ መደረጉን አስታውሷል።CapitalNews
