ሳውዲ አረቢያ በድምሩ በ14 ሀገራት ዜጎች ላይ የብሎክ ቪዛ ማውጣትን በጊዜያዊነት ማገዷን አስታውቃለች። ከነዚህ ሀገራት መካከል ኢትዮጵያን ጨምሮ ሰባት የአፍሪካ ሀገራት ይገኙበታል።
ይህ የቪዛ እገዳ አዲስ የጊዜያዊ የሥራ ቪዛ ማመልከቻዎችን እና በመጠባበቅ ላይ ያሉትንም የሚመለከት ነው የተባለ ሲሆን በውጭ ዜጎች የሥራ ኃይል ላይ የተመሰረቱ የሳውዲ አረቢያ ዘርፎችን እንደሚጎዳ ተገልጿል።
በእገዳው ሰለባ ሆነዋል ከተባሉት የአፍሪካ ሀገራት መካከል ኢትዮጵያ ፣ ግብፅ፣ ናይጄሪያ፣ አልጄሪያ፣ ሱዳን፣ ቱኒዚያ እና ሞሮኮ ይገኙበታል። ከዚህ በተጨማሪ ኢንዶኔዥያ፣ ኢራቅ፣ ዮርዳኖስ፣ የመን፣ ህንድ፣ ፓኪስታን እና ባንግላዲሽ ተካትተዋል።
እነዚህ ሀገራት ከሳውዲ አረቢያ ከፍተኛ የሰው ኃይል ፍልሰትና የገንዘብ ዝውውር ስለሚያገኙ፣ እገዳው ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ጫና ሊያስከትል እንደሚችል ተዘግቧል።
የብሎክ ቪዛ የሳውዲ አረቢያ ቀጣሪዎች ቀድሞ በተፈቀደላቸው ኮታ የውጭ ሠራተኞችን እንዲቀጥሩ የሚያስችል ነው። የሳውዲ አረቢያ መንግስት የቪዛ እገዳውን የጣለበትን ዝርዝር ምክንያት ባይገልጽም፣ ይህ እርምጃ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰራተኞችን ዕጣ ፈንታ አጣብቂኝ ውስጥ ሊጥል እንደሚችል ካፒታል ለመረዳት ችሏል።
