የኢትዮጵያ የልብ ህሙማን ማህበር በ2024 በጀት ዓመት ከ12 ሺህ በላይ የተመላላሽ የልብ ሕክምና ክትትል እና 669 ለሚጠጉ ታካሚዎች ደግሞ የህክምና አገልግሎት መስጠቱን አስታውቋል።
ለታካሚዎች የሰጠው አገልግሎት በገንዘብ ሲተመን ከ250 ሚሊዮን ብር በላይ የልብ ቀዶ ሕክምና እና በ ደም ስር በኩል የሚሰጥ የህክምና አገልግሎት መሆኑን በኢትዮጵያ የልብ ህሙማን ህጻናት መርጃ ማዕከል የህዝብ ግንኙነት እና ኮሙኒኬሽን ክፍል ባልደረባ የሆኑት ዶክተር ዳዊት እሸቱ ተናግረዋል ።
ማዕከሉ ምንም እንኳን ነጻ የህክምና አገልግሎት የሚሰጥ ቢሆንም አንድ ቀዶ ህክምና ለመስራት ተቋሙ የሚያወጣው ወጪ ከ100 ሺህ ብር በላይ እንደሚሆን ተጠቁሟል። አንድ ታካሚ መጀመሪያ ከታየበት ቀን አንስቶ ቀዶ ህክምና እስከሚሰራበት ቀን ድረስ ለዓመታት ወረፋ ሊጠብቅ እንደሚችል ተጠቁሟል።
በተጨማሪም በተያዘው በ2025 ዓመት ከ17,000 በላይ ለሚሆኑ ታካሚዎች አገልግሎት ለመስጠት እንዲሁም 352 የልብ ቀዶ ህክምና እና 334 በደም ስር በኩል የሚሰጥ ህክምና ለመስጠት በዕቅድ መያዙን ተጠቁሟል። በአሁን ሰዓት አጠቃላይ ታካሚዎች ቁጥር 20 ሺህ ሲሆን ወረፋ የሚጠብቁ ታካሚዎች ደግሞ ስምንት ሺህ መሆናቸውን አንስተዋል። ይሁን እና ተቋሙ ለህክምናው የሚያስፈልጉ እቃዎችን ለማሟላት ችግር እንደሆነባቸው ገልጸዋል። በተለይም መድሃኒቶች በበቂ ሁኔታ አለመኖራቸው በታቀደው ልክ ህክምና መስጠት እንዳይቻል ትልቅ ተግዳሮት መሆኑን ዶክተር ዳዊት እሸቱ ጨምረው ብሥራት ሬዲዮ ዘግቧል።
