በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል እየጨመረ የመጣው የኤችአይቪ ሥርጭት አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን የክልሉ ጤና ቢሮ አስታወቀ። ባለፉት ሰባት ወራት ብቻ ምርመራ ከተደረገላቸው ሰዎች መካከል 6.7 በመቶ በደማቸው ኤችአይቪ ተገኝቶባቸዋል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው፤ “የቫይረሱ ሥርጭት ሳናውቀው ችግር ውስጥ እያስገባን ይገኛል” ብለዋል።
መቶ አለቃ ይሳቅ ታንጋ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ፣ የሲዳማ፤ የደቡብና የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልሎችን የሚሸፍነው የደቡባዊ ኢትዮጵያ ኤች አይ ቪ ፖዘቲቭ ማህበራት ጥምረት ዳይሬክተር ናቸው፡፡ በአራቱ ክልሎች ብቻ በየዓመቱ ከ2 ሺህ በላይ አዳዲስ ሰዎች በኤች አይ ቪ ኤድስ አማጭው ተህዋሲ እየተያዙ እንደሚገኙ የተናገሩት የጥምረቱ ዳይሬክተር፤ “የተህዋሲው የሥርጭት መጠን የመጨመር አዝማሚያ እያሳየ ይገኛል፡፡ አሁን ላይ በአራቱ ክልሎች ተህዋሲው በደማቸው የሚገኝባቸው 68 ሺህ 535 ሰዎች አሉ፡፡ ይህም በአገር አቀፍ ደረጃ 11 ነጥብ 4 በመቶ የሚሆን ነው“ ብለዋል፡፡
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሆሳዕና ከተማ እየተካሄደ በሚገኘው የኤች አይ ቪ ኤድስ መከላከል የንቅናቄ መድረክ፤ በተህዋሲው መስፋፋትና አሳሳቢነቱ ላይ እየመከረ ይገኛል፡፡ የመድረኩ ተሳታፊዎች“ በሽታውን አስመልክቶ ቀደም ሲል ይደረጉ የነበሩ እንቅስቃሴዎች ተዳክመዋል፣ቸልተኝነትም በዝቷል“ የሚሉ ሀሳቦችን አንስተዋል፡፡
በክልሉ ባለፉት ሰባት ወራት ብቻ በጤና ተቋማት ምርመራ ከተደረገላቸው ሰዎች መካከል ስድስት ነጥብ ሰባት በመቶ ያህሉ በደማቸው የበሽታው አማጭ ተህዋሲ እንደተገኘባቸው በክልሉ ጤና ቢሮ የኤች አይ ቪ ኤድስ መከላከልና መቆጣጠር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አለምአየሁ ጌታቸው ተናግረዋል፡፡
በክልሉ በ38 የጤና ተቋማት 381 ሰዎች ምርመራ እንደተደረገላቸው የጠቀሱት አቶ አለማየሁ፤ “ከእነኝህ መካከል ስድስት ነጥብ ሰባት ሰዎች በደማቸው የበሽታው ተህዋሲ ተገኝቶባቸዋል፡፡ ቁጥሩ የበሽታው ሥርጭት እያደገ መምጣቱን ያሳያል፡፡ ይህም አሳሳቢ መሆኑንና ከወዲሁ የመከላከል ሥራዎች መሠራት እንደሚገባ ጠቋሚ ነው “ ብለዋል፡፡
@Dw
