የአዲስ አበባ ከተማ ንግድ ቢሮ በምሽት የንግድ እና የትራንስፖርት አገልግሎት እንዲሰጥ ለማድረግ የወጣውን ደንብ ቁጥር185/2017 ከዛሬ ጀምሮ ተግባራዊ ማድረግ መጀመሩን አስታውቋል።
ቢሮው የአዲስ አበባ ከተማ አሁን ከደረሰችበት ኢኮኖሚያዊና ማህበረሰባዊ ለውጥ አንፃር የአብዛኛው ማህበረሰብ የሥራ ባህል እና ፍላጎት በመለወጡ የንግድ ሥራዎችንና አገልግሎቶችን በምሽት መከወን እየተለመደ የመጣውን ተግባር ወጥነትና ቀጣይነቱን ማረጋገጥ ማስፈለጉን አስታውቃል
ለዚህም ደንቡ በመውጣቱን ይህ ደንብ ቀደም ብሎ የከተማ አስተዳደሩ ካቢኔ ያስተላለፈውን ውሳኔ ለማስፈጸም በመሆኑ ከዛሬ መጋቢት 10 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ መደረግ መጀመሩን የቢሮው ኃላፊ ወ/ሮ ሐቢባ ሲራጅ አብራርተዋል፡፡
በመሆኑም በከተማዋ በስፋት እየተከናወነ የሚገኘው መሠረተ-ልማት በኢኮኖሚው ላይ የፈጠረውን መነቃቃት አጠናክሮ ለማስቀጠል፣ የስራ ባህልን ይበልጥ ለማዳበር ፣ የኢኮኖሚ እድገትን ለማፋጠን፣ የከተማዋን ተወዳዳሪነት እውን ለማድረግ ቀን ከሚሰጠው አገልግሎት በተጨማሪ በምሽት የንግድ እና አገልግሎት መስጫ ተቋማት አገልግሎት የሚሰጡበት ምቹ ሁኔታ መፍጠር አስፈላጊ መሆኑን ገልጿል፡፡
በደንቡ የተካተቱ ዋና ዋና ጉዳዮች ማብራሪያ በሁሉም የሚዲያ አውታሮች አማካኝነት ማህበረሰቡ እንዲያውቃቸው እንደሚደረግ እና ደንቡን የማስተዋወቅ ስራ እንደሚሰራም መግለፃቸውን ከቢሮው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
