በእውነታ ብቻ ሳይሆን በሀገር ባሕል ስለምመራ ( ባልመራ እንኳን አክብሮት ስላለኝ ) ባለቤቱ በሕይወት በሌላበት የመረረ ወቀሳ አላቀርብም ። " ምርጥ ነበረ "ም አልለውም ። " አክቲቪስት " ያልኩት በፊት የሚታወቅበትን ድምጻዊነት ትቶ በአክቲቪስትነቱ ስለገፋበት ነው ። በግሌ ሰው ከሞተ በኋላ መወቀስ የለበትም በሚለው አላምንም ። ጥላሁን ገሠሠ ሲሞት ሀገር ፍራሽ አውርዶ እንደተቀመጠለት ሁሉ ሁላችንም ስንሞት በየምንታወቅበት መንገድ መመስገንና መወቀስ አለብን ። ከሞትን በኋላ ተመልሰን የምናስተካክለው ነገር ስላለን አይደለም ። ድሮም ሕይወታችን ለሌላው መማሪያ ነው ።
የሰለሞንን ሞት Zehabesha ላይ ሳነብ ደነገጥኩ እንጂ ደስ አላለኝም ። ወዲያው አዕምሮዬ ላይ የመጡት ቃላት " በቃ !? ለዚሁ ነው !? " የሚሉት ናቸው ። እስከዚህ ድረስ ነው የሰው ልጅ ሕይወት ። መቸም እንደ ሰለሞን ተካልኝ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ ዥዋዥዌ የተጫወተ የለም ። የሰለሞን ነውር ከሕዝብ ጋር የገጠመው ብሽሽቅ ነው ። መረን የለቀቀው የአማራ ጥላቻው ነው ። ማንም የትግራይ ሰው ለፖለቲካው እንደ ኮንዶም ሊጠቀመው ካልሆነ " የእኔ " የሚለው አይመስለኝም ። አሁን የሰለሞን ቤተሰቦች ካሉ ሲሆን በነበረው የሚደሰቱ አይመስለኝም ። ለልጁ ምን ሰጠው ? ጥላቻ ።
ይህን የምጽፈው ከአልጋ ሳልወርድ ነው ። እኔም ራሴ አሁን ከአልጋ ሳልወርድ ሞቼ ፣ ይሄ ያልጨረስኩት ጽሑፍ ተገኝቶ " ስለ ሰለሞን ተካልኝ የጀመረውን ጽሑፍ ሳይጨርስ ሞተ " ሊባልልኝ ይችላል ። የሕይወት ጉዳይ በዚህ ልክ እንዲሰማኝ ነው የምፈልገው ። የእኔ ሕይወት የሌሎች መማሪያ ነው ። አሁን ስለ ሰለሞን ስጽፍ የእኔ መኖር እየተሰማኝ አይደለም ። ተራነቴን ፣ ትንሽነቴን ፣ ኢምንትነቴን ይበልጥ እያስታወስኩ ነው ። እንዳልዘነጋው የምፈልገው የሕይወቴ ክፍል ሟችነቴ ነው ። ትናንትም ዛሬም የሰለሞን አይነት ማንነት ያላችሁ ፣ ባለጊዜነት የሚሰማችሁ ፣ ቋሚ ሰውነት የሚያጓጓችሁ ፣ ከሕዝብ ጋር መበሻሸቅ ውስጥ ያላችሁ የማገናዘቢያ ልቦና ከሰጣችሁ ቆም ብላችሁ አስቡበት ። መቼም ቋሚነት አይሰማችሁ ። መኖር አያጓጓችሁ ። ምንም ቢሆን ከሕዝብ ጋር አትበሻሸቁ ። ሕዝብ ባይወዳችሁ እንኳን አይጥላችሁ ።
እኔ በሰለሞን ተካልኝ ላይ እየፈረድኩ አይደለም ። ስለ እሱ እያሰብኩ ነው ። እሱ ነው እንዲህ የሆነው ። የሆነውን ነው የጻፍኩት ። ነገም በእኔ ላይ እንዲሁ ይባላል ። የሰለሞን ሕይወት ፣ ስቃዩ የሚያሳዝነኝ ዛሬ አይደለም ። በሕይወት እያለም ነው ደጋግሜ የጻፍኩት ። ሰለሞን ሕወሓትን መደገፉ አይደለም ችግሩ ፤ " ትግሬ ካልሆንኩ " ማለቱ ነው ። ሰለሞን በመሞቱ ተጠቀመ እንጂ አልተጎዳም ። ከሚጨንቅ ሕይወት ነው የተገላገለው ። ጥላቻ ስቃይ ነው ። ከዚያ ነው የተገላገለው ። የዳነው ። ስቃይ ነው የቀረለት በቃ ። እስከዚህ ድረስ ነው ።
ከቴዎድሮስ ተ/አረጋይ
በቃ !? ለዚሁ ነው ! ?አክቲቪስት ( ድምጻዊ ) ሰለሞን ተካልኝ በእርግጥም አረፈ
Date:
