በአዲስ አበባ በቅዳሜ ገበያዎች ከተቀመጠው ዋጋ በላይ እንዳይሸጥ የንግድ ቁጥጥር ኮሚቴ በየገበያው መመደቡን የከተማ አስተዳደሩ ንግድ ቢሮ አስታውቋል፡፡
ነጋዴዎች ከተቀመጠላቸው ዋጋ በላይ ሲሸጡ ከተገኝ ያለ ምንም የጽሁፍ ማስጠንቀቂያ ሙሉ በሙሉ ከተመቻቸው ቦታም ጭምር ትስስር እንደሚቋረጥ ቢሮው ገልጿል።
በከተማው በአሁኑ ወቅት 210 ቅዳሜና እሁድ ገበያዎች እየተንቀሳቀሱ ሲሆን፤ ለበዓል 14 ተጨማሪ ባዛሮች ተዘጋጅተዋል ተብሏል።
እነዚህ ጊዜያዊ ገበያዎች በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አስፈላጊ የሆኑ ሸቀጦችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለነዋሪዎች ተደራሽ ለማድረግ ታስቦ የተዘጋጀ ነው።
በተለይም በበዓል ሰሞን በሕብረተሰቡ ላይ ያለውን ጫና ለማቃለል እና የዋጋ ንረቱን ለመቆጣጠር እየተሰራ ነው ሲሉ የቢሮው ኃላፊ ወይዘሮ ሀቢባ ሲራጅ ገልጸዋል።
“ነጋዴዎችን ከአርሶ አደሩ ጋር በቀጥታ የሚያገናኙ ሲሆን ገበያዉ ከ15 በመቶ እስከ 20 በመቶ በሸቀጦች ላይ የዋጋ ቅናሽ በማድረግ የከተማ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ ያደርጋል” ሲሉ ኃላፊዋ ተናግረዋል፡፡
“ይህም ለሸማቾች የዋጋ ቅናሽ ከማድረግ ባለፈ አርሶ አደሩ ምርቱን በተገቢዉ እንዲሸጥና ፍትሃዊ እድሎችን የሚያመቻች ነው” ብለዋል።
