በአማራ ክልል ዋግኽምራ ዞን ከወፍላ፣ ኮረም፣ ዛታና አበርገሌ ወረዳዎች ተፈናቅለው በሰቆጣ ከተማ የሚኖሩ ከ47 ሺህ በላይ ተፈናቃዮች፣ ወደ ቀደመ ቀያቸው እንዲመለሱ የሚጠይቅ ሰላማዊ ሰልፍ በዛሬው ዕለት ተካሂዷል።
ሰልፈኞቹ በጸጥታ ችግር ምክንያት ለከፋ ስደት መዳረጋቸውን ገልጸው፣ ወደ ቀደመ ሕይወታቸው ለመመለስ የታጠቁ ኃይሎችና የሕወኃት የጦርነት ትንኮሳ በአስቸኳይ እንዲቆም ጠይቀዋል።
የተፈናቃዮች ኮሚቴ አስተባባሪ አቶ ያሬድ ከፍያለው ለአሐዱ እንደገለጹት፣ ተፈናቃዮቹ በመጠለያ ጣቢያዎች ውስጥ ለረኃብና ለዘርፈ ብዙ ማኅበራዊ ችግሮች ተጋልጠዋል። በሰልፉ ላይ “ወደ ቀያችን ተመልሰን የመምረጥ መብታችን ይከበር፣ ዳግም ጦርነትና አፈና ይቁም፣ ፍትሕ እንፈልጋለን” የሚሉ መፈክሮች መስተጋባታቸውን አስተባባሪው ተናግረዋል።
ከማለዳው 12 ሰዓት ጀምሮ ለ3 ሰዓታት በተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ የሃይማኖት አባቶችና የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችም ተገኝተዋል ተብሏል።
የዋግኽምራ ዞን ሰላምና ፀጥታ መምሪያ ኃላፊ ሐምሳ አለቃ አዘዘው አዳነ፣ ዜጎች ከመኖሪያቸው የተፈናቀሉት በታጠቁ ኃይሎችና በሕወኃት ትንኮሳ እንደሆነ አስታውሰው፤ ችግሩ በዘላቂነት እንዲፈታና የዓለም ማኅበረሰብ ጉዳዩን እንዲገነዘብ ጠይቀዋል።
የታጠቁ አካላት ወደ ድርድር ጠረጴዛው እንዲመጡ እና ዜጎች ወደ ቀደመ ቀያቸው እንዲመለሱ፣ ሰብአዊ መብታቸው እንዲከበር ሁሉም እንዲተባበርም ጥሪ አቅርበዋል።
አሐዱ ሬዲዮ
#አሐዱ_የኢትዮጵያውያን_ድምጽ
