በአሜሪካ፣ ቴክሳስ ግዛት አርብ ዕለት ባጋጠመ የጎርፍ አደጋ ቢያንስ 24 ሰዎች ሲሞቱ በካምፕ ውስጥ የነበሩ ወደ 25 የሚጠጉ ሴት ታዳጊዎች መጥፋታቸውን ባለሥልጣናት አስታወቁ።
ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ በነጻነት ቀን ያጋጠመውን ይህንን የጎርፍ አደጋ “አስደንጋጭ” እና “አስከፊ ” ብለውታል።
የፌደራል ባለሥልጣናትም እርዳታ እያደረጉ እንደሆነ የቴክሳስ ገዥ ግሬግ አቦት ተናግረዋል።
ምንም እንኳን የግዛቷ ባለሥልጣናት በጎርፉ ምክንያት የገቡበት ያልታወቁ ሰዎችን ቁጥር ባያረጋግጡም ፍለጋው እና የነፍስ አድን ጥረቱ ሌሊቱን መቀጠሉን የግዛቷ ገዥ ገልጸዋል።
የጎርፍ አደጋው መንስዔ ግዛቷ በበርካታ ወራት የምታገኘው የዝናብ መጠን በጥቂት ሰዓታት ውስጥ መዝነቡ እንደሆነ ተገልጿል።
ጎርፉ ድልድዮችን ጠራርጎ ሲወስድ እና በከፍተኛ ፍጥነት የሚጓዝ ጎርፍ መንገዶችን ሲያጥለቀልቅ በማኅበራዊ ሚዲያ የተጋሩ ምስሎች አሳይተዋል።
የቴክሳስ ምክትል አስተዳዳሪ ዳን ፓትሪክ “ጎርፉ ከመከሰቱ በፊት የወንዙ የውሃ ከፍታ ጨምሮ ነበር።
በ45 ደቂቃ ውስጥ፣ ጉዳሉፕ ወንዝ 26 ጫማ ከፍታ ጨምሮ ነበር። አውዳሚ ጎርፍ ነው፤ ሕይወትን እና ንብረትን አጥፍቷል።” ብለዋል።
ፓትሪክ ጨምረውም ” ሕጻናቱ የገቡበት አልታወቀም ማለት ሞተዋል ማለት አይደለም፤ ከግንኙነት መስመር ወጥተው ሊሆን ይችላል” ሲሉ ቤተሰቦችን አጽናንተዋል።
