በኢትዮጵያ ሀገር አቀፍ ደረጃ የመነጽርን ጥራት እና ደረጃ የሚቆጣጠር አካል አለመኖሩን የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጤና ሳይንስ ኮሌጅ አስታውቋል ። በዚህም የተነሳ ዜጎች ጥራቱ የተረጋገጠ መነጽር ስለማያገኙ ለከፋ የዓይን ጤና ህመም እየተጋለጡ መሆኑን ተጠቁሟል።
የኮሌጁ የዓይን ህክምና ትምህርት ክፍል ተባባሪ ፕሮፌሰር ዶክተር ሳዲቅ ታጁ እንደተናገሩት፣ መነጽር በዓይን ጤና ውስጥ እንደ መድሃኒት የሚያገለግል የህክምና ቁስ ቢሆንም፣ ጥራቱንና ደረጃውን የሚለይለት እና የሚቆጣጠርለት አካል በሀገር አቀፍ ደረጃ የለም።
በዚህም ምክንያት ዜጎች ጥራቱ ያልተረጋገጠ ምርት በመግዛት ለተደጋጋሚ ወጪ እና ተጨማሪ የዓይን ችግር እየተጋለጡ ነው ሲሉ ተደምጠዋል።
በተጨማሪም የመነጽር ጥራት ቁጥጥር ባለመኖሩ በሺዎች የሚቆጠሩ የመነጽር ቤቶች እና በየመንገዱ መነጽር የሚያዞሩ ግለሰቦች በመብዛታቸው፣ እንዳሻቸው ሰርተውና ዋጋ ተምነው ለተጠቃሚው እያቀረቡ ነው ብለዋል። ይህ ደግሞ ብዙዎችን ለከፋ የዓይን ጤና ችግር እያጋለጠ ነዉ ሲል ኢፕድ ባለሞያውን ዋቢ አድርጎ ዘግቧል ።
መንግስት በዚህ ጉዳይ ላይ ትኩረት ሰጥቶ ሊሰራ እንደሚገባ የተገለፀ ሲሆግ መነጽር እንዴት መሰራቱና መገጣጠም እንዳለበት፣ የት ቦታ መሰራቱ እንዳለበት፣ በምን ያህል የጥራት ደረጃ መሰራቱ እንዳለበት፣ በምን አይነት መልኩ መሸጥ እንዳለበት የሚሉትን ጉዳዮች ለይቶ የሚሰራ አካል መመደብና አፈጻጸሙን መቆጣጠር ያስፈልጋል ተብሏል።
Source: capitalethiopia
