ቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል በኢትዮጵያ የመጀመሪያውን የጉበት ንቅለ ተከላ ህክምና በቅርቡ እንደሚያካሂድ አስታውቋል።
የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም የህክምና ኮሌጅ የኮሙኒኬሽን ኃላፊ አቶ ንዋይ ፀጋዬ፥ የሆስፒታሉ ከፍተኛ የህክምና ባለሙያዎች ልዑክ በጉበት ንቅለ ተከላ ህክምና ከፍተኛ ልምድ ባለው የካሊፎርኒያው ፓሲፊክ የህክምና ማዕከል ለሳምንታት የቆየ የምልከታ ስልጠና ሲያደርግ መቆየቱን ገልፀዋል።
በትውልደ አትዮጵያዊቷ አሜሪካዊት የጉበት ንቅለ ተከላ የህክምና ባለሙያ ዶ/ር ቅድስት ኪዳነ ይልማ አመቻችነት የተካሄደው መርሐ ግብር፥ ኢትዮጵያ የመጀመሪያውን የጉበት ንቅለ ተከላ አገልግሎት ለማከናወን በምታደርገው ጥረት ውስጥ ትልቅ ምዕራፍ ነው ብለውታል።
የባለሙያዎች ቡድን አባላቱ በርካታ የጉበት ንቅለ ተከላ ሂደቶችን የተመለከቱ ሲሆን ከዋነኛ የንቅለ ተከላ ቀዶ ጥገናሐኪሞች የተግባር ስልጠና እና የዕለት ተዕለት ምክር ማግኘታቸውንም ነው የተናገሩት።
ቡድኑ በቆይታው ንቅለ ተከላ የሚያስፈልጋቸውን ታካሚዎች የጤና ደረጃ፣ የለጋሾች ልየታ እና በህክምናው ዙሪያ ያሉትን ስርዓቶች በተመለከተ አስፈላጊ እውቀት ማግኘቱን ጠቁመዋል።
ሆስፒታሉ በቅርብ ጊዜ ውስጥ በበቂ ዝግጅት ወደ ሥራ ሲገባ ለጉበት ንቅለ ተከላ ህክምና ውጭ ሀገር መሄድን እንደሚያስቀር አመላክተዋል።
(አራዳ ኤፍ ኤም)
