ተስፋሁን ታመነ
አሁን ላይ ኑሮውን በዲላ ከተማ ሀሮወላቡ ክፍለ ከተማ ውስጥ ያደረገው የ25 ዓመት ወጣት ተስፋሁን ታመነ ይባላል፡፡ ተስፋሁን ትምህርቱን 8ኛ ክፍል ደርሶ ያጠናቀቀ ሲኾን፣ ባለትዳርና የአንዲት ሴት ልጅ አባትም ነው። የቤተሰቡ ራስ በመኾኑ ደግሞ አሁን ላይ በርካታ ኃላፊነቶች አሉበት፡፡ ነገር ግን ሥራ ማግኘት ባለመቻሉ ሳቢያ እሱም ኾነ ቤተሰቡ ሥነ ልቦናዊ እና ኢኮኖሚያዊ ቀውሶች ሊገጥማቸው ግድ ኾኗል።
ከዕለታት በአንዱ ታዲያ፣ ተስፋሁን ከከፍታ የፕሮጀክት ቡድን ጠቃሚ መረጃዎችን ሰማ ፤ አጋዥ የምክር አገልግሎቶችንም አገኘ፡፡ እርሱ እንደሚለው ከኾነ በተለይ የሕይወት ክህሎትን በማዳበር፣ በጾታዊ እና ሥነ ተዋልዶ ጤና፣ በንግድ ልማት ክህሎት፣ ገንዘብን የተመለከተ ግንዛቤ ፣ ንቁ ዜጋ በመኾን ረገድ እንዲሁም ውጤታማ የሥራ ልምድ ማዳበር ላይ ያተኮሩ ተከታታይ ሥልጠናዎች በወጣቶች ማዕከላት ላይ እንደተጀመረ ሰማ። ሰምቶም ሥልጠናውን ተቀላቀለ፡፡ በዚህም መሠረት በከፍታ የሕይወት ክህሎት ሥልጠናን ከተከታተሉት ሰልጣኞች መካከል አንዱ ለመኾን እንደበቃ ይገልጻል፡፡
‹‹ይህ ጠቃሚ ሥልጠና እንዴት ወደ ሥራ መስመር መግባት እንዳለብኝ ፈር ቀዶልኛል›› የሚለው ተስፋሁን፣ ‹‹በተጨማሪም ሥራ ለማግኘት ተቀምጦ መጠበቅ አልያም ማመልከቻ ማስገባት እና የማመልከቻውን ምላሽ መጠበቅ ብቻ እንደሌለብኝ ተረድቻለሁ፡፡ በዚህም የተነሣ የአመለካከት ለውጥ እንዳመጣ እና በግሌ መሥራት ስለምችላቸው ሥራዎች እንዳስብ እና እንዳቅድ አድርጎኛል›› በማለት ይናገራል።
ኾኖም በዚህ መልክ ‹‹የራሴን ሥራ ለመጀመር አስቤ እንደ አንድ አማራጭ መንገድ ላይ ጫማ በመጥረግ ሥራ (በተለምዶ ሊስትሮ) ለመሠማራት ብወስንም ፣ ሥራውን ለማከናወን አስፈላጊ ቁሳቁሶችን ለመግዛት ገንዘብ የሌለኝ በመኾኑ በእጅጉ ጭንቀት ላይ ወድቄ ነበር›› ይላል፡፡
ይኽ ጭንቀቱ እንዴት መፍትሔ እንዳገኘ ሲናገርም ‹‹…ከዚያም በከፍታ ወጣቶች ጥምረት ድጋፍ በኩል የሚያስፈልገው ተሟልቶልኝ ሥራ ለመጀመር በቃሁ፡፡ በዚህ አጋጣሚ ሥራው ለመጀመር ያስቻለኝን መሣርያዎች ለሰጡኝ የከፍታ ሰራተኞች ማመስገንና እውቅና መሥጠት እፈልጋለሁ፡፡›› በማለት ነው፡፡
በአጠቃላይ አሁን ላይ እጅግ ደስተኛ መኾኑን የሚናገረው ተስፋሁን ታመነ ፣ ‹‹ራሴን እና ቤተሰቤን ለመደገፍ ጠንክሬ በመሥራት ላይ እገኛሁ፡፡ ይኽንንም ጥረቴን ከፍ ለማድረግ ዕቅዱ አለኝ›› በማለት ስለ ሁሉም እግዚአብሔርን ያመሰግናል፡፡ በመጨረሻም ‹‹ለከፍታ ሰራተኞች ደግሜ ምሥጋናዬን ማቅረብ እወዳለሁ፡፡›› በማለት ሐሳቡን ይቋጫል።
———-
ቅጽ 6 ግዮን ቁጥር 216 ጥቅምት 2 ቀን 2017 ዓ.ም
