በማይክሮ አልጌ ባዮቴክኖሎጂ ዘርፍ በዓለም አቀፍ ደረጃ ግንባር ቀደም ምሁር የነበሩት አመሃ በላይ (ዶ/ር) በተወለዱ በ79 ዓመታቸው፣ የካቲት 15 ቀን 2018 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል።
ዶ/ር አመሃ የቀድሞው ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ምሩቅ ሲሆኑ፣ የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ደግሞ ከዩናይትድ ኪንግደም አግኝተዋል።
ወደ ሀገራቸው በመመለስም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለ13 ዓመታት በመምህርነትና በባዮሎጂ ትምህርት ክፍል ኃላፊነት አገልግለዋል።
በሙያ ሕይወታቸው ከፍተኛ ዝና ያተረፉት፣ በካሊፎርኒያው “Earthrise Nutritionals” ተቋም ውስጥ ለ26 ዓመታት በከፍተኛ የቴክኖሎጂ መኮንንነት (CTO) በሰሩበት ወቅት ነው።
በዘርፉ ባላቸው ጥልቅ ዕውቀትና ለስፒሩሊና ኢንዱስትሪ ባበረከቱት አስተዋጽኦም “ሚስተር ስፒሩሊና” (Mr. Spirulina) የሚል ስያሜ እስከማግኘት ደርሰዋል።
ዶ/ር አመሃ በላይ ከዓለም አቀፍ ሥራቸው ባሻገር፣ ለሀገራቸው ኢትዮጵያ ባላቸው ጥልቅ ፍቅር ይታወቃሉ። የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ እና ዘላቂ ልማት ምክር ቤት መሥራች በመሆንም አገልግለዋል።
በተለይም በጣና ሐይቅ፣ በአባያ ሐይቅና በአዋሽ ወንዝ ላይ የተከሰተውን አደገኛ የእንቦጭ አረም ለመከላከል በሚደረገው ሳይንሳዊ ጥረት ውስጥ በንቃት ተሳትፈዋል።
የዶ/ር አመሃ በላይ የቀብር ሥርዓት ቅዳሜ፣ የካቲት 21 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚፈጸም ታውቋል።
