የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ቴህራን ድርድሩን ብትክድም ንግግሮች እየተካሄዱ መሆናቸውን አጥብቀው ገልጸዋል።
ኢራን በሆርሙዝ የባህር ሰርጥ እና በኒውክሌር መርሃ ግብሯ ላይ ስምምነት ላይ ለመድረስ የመጨረሻ ዕድል እንዳላት ተናግረዋል።
ትራምፕ በዋይት ሃውስ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ በሳዑዲ ዓረቢያ፣ በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ፣ በኳታር እና በሌሎች አገሮች ጥያቄ መሠረት ከኢራን ጋር ድርድሩን ለመቀጠል መስማማታቸውን ተናግረዋል።
የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከዋሽንግተን ጋር ድርድር እየተካሄደ መሆኑን ቢያስተባብልም፣ ትራምፕ ግን ድርድሩ መቀጠሉን አረጋግጠዋል። ‹‹አሁን እያወራን ነው ››ብለዋል።
ፕሬዝዳንቱ አክለውም ‹‹ይህ ለእነሱ ጥሩ ሰነድ ለመፈረም የመጨረሻ ዕድል ነው›› ብለዋል። የመጨረሻውን ዕድል ሁሉ ልሰጣቸው እፈልጋለሁ ሲሉም ተናግረዋል።
ድርድሩ ትኩረት ያደረገው የሆርሙዝ የባህር ሰርጥን ዳግም በመክፈት ላይ ሲሆን፤ትራምፕ ይህ ‹‹ቃል በቃል ነገ ሊሆን ይችላል››ብለዋል። የኢራን ከኒውክሌር ነፃ መሆን ግን ‹‹ ትንሽ ጊዜ ሊወስድ ይችላል››ብለዋል።
ዋሽንግተን እና ቴህራን አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ድንገተኛ ጥቃት ከሰነዘሩበት ከየካቲት 21 ጀምሮ በጦርነት ላይ ናቸው። ሆኖም ለወራት የተካሄደው አልፎ አልፎ የሚቆራረጥ ዲፕሎማሲ አንጻራዊ መረጋጋት የሰፈነባቸው ወቅቶችን ፈጥሯል።
ከአምስት ወራት በላይ በኋላም ቢሆን ኢራን በሚሳኤልና በድሮን በክልሉ በሚገኙ የአሜሪካ እና የባልደረቦቿ ኢላማዎች ላይ ጥቃት የመሰንዘር አቅሟን እንደጠበቀች ሲሆን፥የዩራኒየም ክምችቷንም ይዛ ቀጥላለች።
ኢራን በበኩሏ በአሁኑ ወቅት ከአሜሪካ ጋር ድርድር እያደረገች እንዳልሆነ ገልጻለች።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ እስማኤል ባጋኢ ‹‹የእኛ ድርድር ወሳኝ በሆነው የነዳጅ መተላለፊያ በሆርሙዝ የባህር ስርጥ በኩል ያለውን ማለፊያ ደኅንነት ለማረጋገጥ ከኦማን ጋር ነው››ብለዋል።
