የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን 75ኛ ዓመት የአልማዝ ኢዩቤልዩ በዓል ማክበር የሚያስችለውን ዝግጅት ማጠናቀቁን እና ወደራስ ገዝነት ለመሸጋገር እያከናወናቸው ባሉ ተግባራት ዙሪያ ለመገናኛ ብዙኃን መግለጫ ሰጥቷል።
ዩኒቨርሲቲው ከተቋቋመበት ከታሕሳስ 1943 ዓም ጀምሮ በሰው ሃይል ልማት፣ በጥናትና ምርምር ዙሪያ የመሪነት ሚናውን እየተወጣ እንደሚገኝ፤ የዩኒቨርሲቲው ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) ተናግረዋል።
የኢዩቤልዩ በዓሉ የሚከበረው ዩኒቨርሲቲው ያበረከተውን አስተዋጽኦ በመዘከር፤ በቀጣይ የሚሰሩ ሥራዎችን ለማጠናከር በማለም ነው ብለዋል።
በዚሁ መሠረት ዩኒቨርሲቲው ያበረከተውን አስተዋጽኦ በመጽሐፍ ሰንዶ ይፋ የማድረግ፣ ዘጋቢ ፊልም፣ የአካዳሚክ ሴሚናሮች፣ የፓናል ውይይቶች፣ በዓሉን ምክንያት በማድረግ የበጎ ፈቃድ ሳምንት መርኃ ግብሮች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።
አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ፣ በኢትዮጵያ የሚገኝ የመጀመሪያውና ትልቁ የመንግሥት የከፍተኛ ትምህርት ተቋም ነው።
“ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ አዲስ አበባ” በመባል ይታወቅ የነበርም ሲሆን በኋላም የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ የሚል ስያሜ ይዟል፡፡ የዘውዳዊው መንግሥት ሥርዓት ከተገረሰሰ በኋላ የተመሠረተው ወታደራዊ መንግሥት(ደርግ) አሁን በሚጠራበት ሥሙ ሰይሞታል።
ታሕሳስ 1943 ዓ.ም የተመሰረተው አዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ 50 ተማሪዎችን በማስተማር ሥራውን የጀመረ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅት ከ170 በላይ ሙሉ ፕሮፌሰሮች፣ ከ10 ሺሕ በላይ የድህረ ምረቃ ተማሪዎችን የማስተናገድ አቅም መፍጠሩን ከዩንቨርስቲው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በኩልም በየዓመቱ ከ1 ሚሊዮን በላይ ዜጎች ሕክምናና እንክብከቤ እንደሚያገኙ የዩንቨርሲቲው መረጃ ያሳያል።
አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዋና አስተዳደሩን ስድስት ኪሎ በሚገኘው በዋናው ግቢ ያደረገ ሲሆን፤ በአምስት ኪሎ (የቴክኖሎጂ ፋኩለቲ-ሰሜን)፣ በአራት ኪሎ የሳይንስ ፋኩልቲ፣ በስድስት ኪሎ (የቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ፋኩልቲ እንዲሁም፤ የኢንፎርማቲክስ ፋኩልቲ)፣ በጥቁር አንበሳ (የሕክምና ፋኩልቲ) በልደታ (የቴክኖሎጂ ፋኩለቲ-ደቡብ)፣ በብሔራዊ (የአዲስ አበባ ንግድ ስራ ኮሌጅ)፣ በሚኒሊክ (የያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት)፣ የጥርስ ሕክምና ትምህርት ቤት፣ እንዲሁም በደብረዘይት ከተማ የእንሰሳት ህክምና ፋኩልቲን ያስተዳድራል።
አሐዱ ራዲዮ
