ቴህራን አርብ ዕለት በደቡባዊ ኢራን አካባቢ የአሜሪካን ኤፍ-15ኢ ተዋጊ ጄትን መትታ ከጣለች በኋላ አውሮፕላኑ ውስጥ የነበረን አንድ አሜሪካዊ ለማግኘት ሁለቱ አገራት የሚያደርጉት ሩጫ ቀጥሏል።
የኤፍ-15ኢ ተዋጊ ጄት አብራሪ በአሜሪካ መገኘቱ የተገለጠ ቢሆንም የመሣሪያ ሥርዓቱን የሚቆጣጠረው ባልደረባው ግን አሁንም እንደጠፋ ነው።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ኢራን በባሕረ ሰላጤው ላይ ሌላ የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላን መትታ መጣሏን አስታውቃለች።
የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ኤ-10 ዋርትሆግ የተባለ አውሮፕላን መጀመርያ ተመትቶ የወደቀውን ተዋጊ ጄት ፍለጋ ላይ እያለ ተመትቶ መውደቁን ዘግበዋል።
የዋርትሆግ አብራሪ በባሕረ ሰላጤው አካባቢ ከአውሮፕላኑ ዘሎ ከወጣ በኋላ መገኘቱን የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ዘግቧል።
ኢራን የአሜሪካ የጦር አውሮፕላኖች ላይ ጥቃት የሰነዘረችው የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት አገራቸው በኢራን ሰማይ ላይ የበላይነት እንዳላት እና የቴህራንን የአየር መቃወሚያ ማንኮታኮታቸውን ከተናገሩ ከአራት ቀናት በኋላ ነው።
ሄግሴት የአሜሪካ አየር ኃይል አሁን ዝግ ብሎ የሚበረውን ቢ-52 ቦምብ ጣይ በኢራን ሰማይ ላይ ማብረር ይችላሉ ሲሉ ተናግረው ነበር።
አሜሪካ በኢራን ላይ የከፈተችውን ጦርነት ተከትሎ እስካሁን ድረስ 13 ወታደሮቿ ሲገደሉ 365 ደግሞ ቆስለዋል።
የአሜሪካ ፕሬዚዳንት በኢራን ተመትቶ የወደቀው አውሮፕላን በሁለቱ አገራት መካከል የሚካሄደውን ድርድር አይጎዳውም ሲሉ ተደምጠዋል።
ነገር ግን ይህ እየተፈለገ ያለው አሜሪካዊ በኢራን እጅ ከወደቀ በፍጥነት ይቀየራል።
ክፉኛ ተንኮታክቷል የተባለው የኢራን አየር መቃወሚያም አሁንም ለአሜሪካ የፖለቲካ እና የጦሩ ራስ ምታት መሆኑንም አሳይቷል።
