በካናዳ በተካሄደው ዓለም አቀፍ የሮቦቲክስ ውድድር ላይ የተሳተፉት የኢትዮ ሮቦቲክስ ታዳጊዎች 3ኛ በመውጣት አገርን የሚያኮራ አስደማሚ ድል አስመዝገቡ።
ከውድድሩ አስቀድሞ በ”ታዲያስ አዲስ” ፕሮግራም የአውሮፕላን ቲኬት እና የሆቴል ወጪ ድጋፍ በተደረገለት ተማሪ አማካኝነት የተገኘው ይህ ድል፣ የኢትዮጵያን ስም በዓለም አቀፍ መድረክ በድምቀት ማስጠራት ችሏል።
ኢትዮ ሮቦቲክስ የትምህርትና ውድድር ማዕከል ላለፉት 15 ዓመታት ታዳጊና ወጣቶችን በኮዲንግ፣ ዲዛይኒንግ እና ኢንጂነሪንግ በማሰልጠን ለቴክኖሎጂው ዓለም ሲያዘጋጅ የቆየ ተቋም ነው።
በአዲስ አበባ 4 ማዕከሎችን ከፍቶ ስልጠናውን በመስጠት ላይ የሚገኘው ማዕከሉ፣ በቀጣይ ወደ ኮሌጅ ደረጃ ለማደግ በሂደት ላይ መሆኑ ተገልጿል።
