ኢትዮጵያ እና ኬንያ ለሁለት ዓመታት በዘለቀ ድርድር በአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጠና ማዕቀፍ የሁለትዮሽ የንግድ ልውውጥን ለማቀላጠፍ የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል።
በዚህም መሰረት በሞያሌ ድንበር ላይ ለሚደረጉ የሸቀጦች ንግድ የመጀመሪያ ጣሪያ 1 ሺህ የአሜሪካ ዶላር እንዲሆን ተወስኗል።
በሞምባሳ የተጠናቀቀው ይህ ስምምነት የንግድ ሂደቶችን በማቅለል የድንበር ማህበረሰቦችን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ለማሳደግ ያለመ ነው።
በስምምነቱ የኢትዮጵያ የድንበር ንግድ ዞን ከሞያሌ በ50 ኪሎ ሜትር እንዲሁም የኬንያ ደግሞ በ100 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚወሰን ሲሆን ነጋዴዎችም በጋራ በተስማሙበት የምርት ዝርዝር መሰረት እስከ 1 ሺህ የአሜሪካ ዶላር የሚደርስ የንግድ ልውውጥ በወር እስከ አራት ጊዜ ድረስ ማካሄድ ይችላሉ ተብሏል።
ይህ ስምምነት የንግድ ዋጋ ጣሪያዎችን፣ የጉዞ ድግግሞሽን እና የድንበር ንግድ ዞኖችን የመሳሰሉ ጉዳዮችን በመዳሰስ ለሁለት ዓመታት በዘለቀ ድርድር የተገኘ ውጤት ነው።
በኬንያ እና ኢትዮጵያ መካከል ያለውን የንግድ ግንኙነት ጠቀሜታ የሚያሳዩ የቅርብ ጊዜ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት እ.ኤ.አ በ 2023 ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ ለኬንያ ትልቁ የኤክስፖርት መዳረሻ ነበረች።
ኬንያ ወደ ኢትዮጵያ በላከቻቸው ሸቀጦች 86.2 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ያገኘች ሲሆን ከኢትዮጵያ ወደ ኬንያ የገቡት ምርቶች በዋናነት ቡና፣ ሻይ፣ ህይወት ያላቸው እንስሳት እና የዘይት እህሎች ሲሆኑ መጠናቸው 36.7 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር መድረሱ ይታወቃል።
CapitalNews
