በትግራይ ክልል ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ የጀርመን ዜና ወኪል ከስፍራው አንድ ዘገባ አሰራጭቷል፡፡ በመቀሌ ነዋሪ የሆኑ አንዲት ለዜና አውታሩ ሲናገሩ ‹‹አሁን ላይ ሆነን ምንም ማቀድ አንችልም፡፡ አዲስ ጦርነት ነገ ሊጀመር ይችላል፡፡›› ያሉ ሲሆን ነዋሪው በዚህ የተነሳ ከፍተኛ ፍርሀት ውስጥ መውደቁን አስረድተዋል፡፡
ጨምረውም ‹‹ኑሮ በጣም እየተወደደ ነው፡፡ እኛ ሰላማዊ መፍትሄ መጥቶ ወደስራችን መመለስና ህይወታችንን መልሰን መገንባት ነው የምንፈልገው›› ብለዋል፡፡
እንደዘገባው በህወሀት ውስጥ የተፈጠረውን ክፍፍል ተከትሎ የትግራይ መከላከያ ሀይል(ቲዲኤፍ) ዋና አዛዥ የነበሩት ታደሰ ወረደ የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝደንት ሆነዋል፡፡፡
እሳቸው በህዝቡ ዘንድ ያለውን ስጋት በማጣጣል ‹‹ጦርነት አይኖርም፡፡ ከትግራይ በኩል ምንም አይነት ቀስቃሽ ሁኔታ የለም›› በማለት እየተናገሩ መሆናቸውንም አስረድቷል፡፡
ዘገባው ሲቀጥል በሌላ በኩል የህወሀት ሊቀመንበር የሆኑት ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ደግሞ በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት ለተፈጠረው ችግር ፖለቲካዊ መፍትሄ እንዲፈለግ እያሳሰቡ መሆናቸውን ገልጿል፡፡
የፌዴራል መንግስቱና አጋሮቹ ለጦርነት እያደረጉ ካለው ዝግጅት እንዲቆጠብ አለም አቀፉ ማህበረሰብ ጫና እንዲያደርግበት ጥሪ ማቅረባቸውንም አስረድቷል፡፡
ይሁንና እነዚህ ሁሉ የመቀሌ ነዋሪዎችን ስጋት እንዳልቀረፉ ገልጿል፡፡ አንድ የከተማው ነዋሪ ሲናገሩ ‹‹ህዝቡ አሁን ከባንክ ገንዘብ እያወጣ ነው፡፡
እንደጤፍ የመሳሰሉ እህሎችም ከመጋዘን እያለቁ ነው›› ያሉ ሲሆን ለሁለቱም የህወሀት አንጃዎችም መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በመልእክታቸውም ‹‹ሁለቱም የህወሀት አንጃዎች ወይ ስልጣን ይልቀቁ፣ አልያም ተፅእኗቸውን ተጠቅመው ከማእከላዊው መንግስት ጋር ይህንን ቀውስ ለማስወገድና ጦርነትን ለማስቀረት ይስሩ›› ማለታቸውን ዘገባው ጠቅሷል፡፡
በሌላ በኩል በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል ድጋሚ ጦርነት ይቀሰቀሳል የሚል ስጋት እንዳለ የጠቀሰውዘገባው በዚህ ጉዳይ የጀርመን አለም አቀፍና የደህንነት ጉዳዮች ኢኒስቲትዩት የአፍሪካ ጉዳዮች ኤክስፐርት የሆኑትን ጊርት ኩርዝ ማነጋገሩን አስታውቋል፡፡
ኩርዝ ለዜና አውታሩ በሰጡት ማብራሪያ ሁለቱ አገራት ሙሉ ጦርነት ውስጥ ይገባሉ የሚል እምነት እንደሌላቸው ጠቅሰው ይሁንና በውክልና የሚደረግ ግጭት እንደሚኖር አስረድተዋል፡፡
ዘገባው አያይዞም ኤርትራ ወደ ኢትዮጵያ ግዛት 10 ኪሎሜትር መግባቷንና ጦር እያሰለጠነች መሆኑን ዘገባው ጠቅሷል።
