ጤና አዳም፦ ቅጠሉም ሆነ ፍሬው ለሆድ መታወክ ፣ ለቁርጥማትና ለሌሎች መሰል ሕመሞች መድኃኒት ነው።
ዳማከሴ፦ ለጉንፋን ፣ ለከባድ ራስ ምታት (ማይግሬን) በአፍንጫ ተስቦ የሚወሰድ ፣ ለመተንፈሻ ቧንቧ ችግርና አጠቃላይ ለምች ፍቱን መድኃኒት ነው።
ሬት፡- ቅርፊቱ ተልጦ የሚገኘው የውስጡ ዝልግልግ የማር ወለላ የመሰለው ነገር ከሌላ ምግብ ጋር አዋሕዶ በመምታት የከሱ ሕፃናት ቢመግቡት ወዲያውኑ ያፋፋቸዋል ፣ ለቁስል ቢቀቡት ወዲያው የመፈወስ ኃይል አለው ፣ ለፎረፎር ቢቀቡት፣ የስኳር በሽተኞችና የደም ግፊት ችግር ያለባቸው ሰዎች አድርቀው ፈጭተው እንደ ሻይ አፍልተው ቢጠጡት የመፈወስ አቅም አለው። ቅርፊቱ ስጋ በልቶ አልፈጭ ብሎት ሆዱ የታወከ ሰው ወቅጦ ቀቅሎ ቢጠጣው ይድናል።
አርማ ጉሳ፦ አረንጓዴውን ቅጠል በማድረቅ ወቅጠው እንደ ሻይ ለረጅም ጊዜ በመጠጣት የስኳር ህመምተኞች በደማቸው ውስጥ ያለው የስኳር መጠን ፈጥኖ የማውረድና የመቀነስ አቅም አለው። ቅጠሉን ደግሞ በአረንጓዴነቱ ወቅጠው ጨምቀው ቢጠጡት ከቁርጥማት የመፈወስ ኃይልና የምግብ አፒታይት የመክፈት ኃይል አለው።
ነጭ ሽንኩርት፦ ለደም ዝውውር ፣ ለጨጓራ ፣ ለውስጥ ካንሰር፣ ለመተንፈሻ አካል፣ ለወሲብ ማነቃቂያነት እና በሰውነት ውስጥ ምግብ እንዲንሸራሸር ፍቱን መድኃኒት እንደሆነ አዋቂዎች አብነት በመጥቀስ ይናገራሉ።
የኮክ ዛፍ ቅጠል፦ የጋማና የቀንድ ከብቶች በድንገት ሲታመሙም ሆነ ሰዎች በድንገተኛ በሽታ ሲያዙ ከጤና አዳም ጋር ተወቅጦና ተጨምቆ ሲጠጡት ከህመማቸው ይፈወሳሉ።
ግራዋ፡- ቀን ተመርጦ 7 ቅጠሉ ተቀንጥሶ በሰው እጅ መድኃኒት ለበላ ሰው ቢያጠጡት የመፈወስ ኃይል አለው ፣ እንዲሁም በግራዋ የታጠበ እቃ(እንስራ) ሽታን የሚያመጡ ባክቴሪያዎችን ያጠፋል። ከዚህ በተጨማሪም ግራዋ የተተከለበት ቦታ እባብ ፈፅሞ አይኖርም።
የነጭ_ባሕርዛፍ_ቅጠል፦ ቅጠሉን በውሃ ተፈልቶ ቢታጠኑት የመተንፈሻ አካል ችግርም ሆነ የትኛውም የጉንፋን ዓይነትን ያለ ኪኒን በሁለት ቀን ውስጥ ፈውስ ያገኛል።
ቀይ ሽንኩርት፦ ለአጠቃላይ ጤንነትና ለደም ዝውውር ጠቃሚ ከመሆኑም ባሻገር የዘር ፈሳሽ እጥረት ላጋጠማቸው ሰዎች በብዛት ለማመንጨት እንደሚያገለግል አባቶች ይናገራሉ ፤ ኮረሪማና ቆንዶ በርበሬ እነዚህ በአንድ ላይ ተቀምመው ለራስ ምታትና ለሆድ ቁርጠት ፍቱን መድኃኒት ናቸው።
እንስላል፦ በውሃ ተቀቅሎ ሲጠጣ የተዘጋ የሽንት ትቦ ይከፍታል።
የምድር እምቧይ ስሩ /አሚቾው/፡- ተወቅጦ የታመሙ ከብቶች እንዲጠጡት ሲደረግ ከብቶቹ ይድናሉ።
ቀጋ፡- ለሆድ ሕመም መድኃኒትነት ያገለግላል፡፡
የእንጆሪ ቅጠል፡- በንፅህና ደርቆ ተወቅጦ በሻይ መልክ ተፈልቶ ቢጠጣ የስኳር ህመምን ይቀንሳል።
ፌጦ፦ ለድንገተኛ ህመምና ውጋት ተወቅጦና ተበጥብጦ በመጠጣት ከህመም መፈወስ ይቻላል።
ቀበርቾ /ቾሳ/፡- ከስራስር ክፍል የሚመደብ ሲሆን አገልግሎቱም ለድንገተኛ ህመም ፣ ውጋት ወዘተ በማኘክ የሚወሰድ ፈዋሽ መድኃኒት ነው።
ጣዝማ ማር፦ ከመሬት ተቆፍሮ የሚገኝ የማር ዓይነት ሲሆን ከነጭ አዝሙድና ኮረሪማ ጋር በመቀላቀል ጠዋት ጠዋት ሁለት ማንኪያ በመውሰድ ከሳል ፣ ከአስም ፣ ከቁርጥማት ወዘተ ህመም መገላገል ይቻላል። ይህንን መድኃኒት የወሰደ አንድ ሰው መድኃኒቱ እንዲሠራ ቢያነስ ከአንድ ሰዓት እስከ አንድ ሰዓት ተኩል ጊዜ ድረስ ሌላ ተጨማሪ ነገር እንዳይጠጣ ይመክራል።
ሎሚ፡- ለብዙ ዘመናት ከምግብ መመረዝና ተያያዥነት ካላቸው ሌሎች ምክንያቶች የሚከሰት የሆድ በሽታ ለመፈወስ ሲጠቀሙት የቆየ ባህላዊ መድኃኒት ነው።
ልምጭ፦ ከድንገተኛ ህመም ፈዋሽ ሲሆን የጥርስ መፋቂያ ዓይነትና ለብዙ በሽታዎች ፍቱን መድኃኒት ነው፤ ከበሽታዎቹም መካከል የአፍንጫ ነስርና ላለበት ሰው ነስሩን ለማስቆም ቅጠሉን በመበጠስና በማሸት ቢያሸቱት ፍቱን መድኃኒት ነው።
እንቆቆና መስመስ፦ ለሆድ ትላትልና መሰል በሽታዎች ተፈጭቶና ተበጥብጦ ከኮሶ ጋር በመደባለቅና በመጠጣት ለኮሶ ትልና መሰል የሆድ ህመም መድኃኒት ነው።
የጥቁር ገብስ አረቄ፡- የጥቁር ገብስ አረቄ ለአስም በሽታ ጠዋት ጠዋት ሁለት መለኪያ ቢወስዱት በሽታውን ማስታገስ ይቻላል።
ሰንሰል እና_አግራ፦ ሰንሰል ከሀገር በቀል መድኃኒት ውስጥ የሚካተት ሲሆን ቅጠሉን በመበጠስ ተወቅጦ በሻይ ብርጭቆ አንድ በባዶ ሆድ ሲጠጡበት በወፍ በሽታ ለተጠቃ ሰው ፍቱን መድኃኒት ነው።
የእንሰት ስር(አምቾ)፡- ከውስጥ አካሉ የሚገኘው ውሃ እና አሚቾው ተቀቅሎ ደጋግሞ መብላት ከወፍ በሽታ ይፈውሳል እንዲሁም እንዲመግል የተፈለገ የተጎዳ የሰውነት አካልም ሆነ በሰውነት የወጣ ማንኛውም እባጭ መግል ሆኖ እንዲፈነ/እንዲወጣ የእንሰት አምቾ ተደጋግሞ ይበላል ፣ የተሰበረ አጥንት በወጌሻ ማጀል ሲያስፈልግ የተሰበረው ቦታ ለማለዘብ (ለማለስለስ) አምቾውን በእርጎ እያማጉ ደጋግሞ መብላት ነው ፣ በጠቦት ሾርባ ደጋግሞ መብላት በመኪናም ሆነ በጦር ሜዳ ስጋው የተቦጨቀ ወይም አጥንቱ ላይ አደገኛ ስብራት ያጋጠመው ቁስሉ እንዲሽር(እንዲጠገን) ያደርጋል።
ኮሶ፡- የደረቀ የኮሶ ዛፍ አበባ ከእንቆቆና መስምስ ወቅጦ በብርጭቆ በመጠጣት የሆድ ውስጥ ጥገኛ ትላትልን ጠራርጎ ማስወጣት ይቻላል።
ሽፈራው:- የዚህ ዛፍ ቅጠል የማያድነው በሽታ የለም ይባላል የስኳር መጠንን ይቀንሳል ፣ የደም ግፊትን ይቀንሳል ፣ የደም ዝውውርን ያቀላጥፋል ቅጠሉን…. እንደ ሻይ ተፈልቶ ፣ ዱቄቱ ተወቅቶ በውሃ መጠጣትም ይቻላል ፤ እንዲሁም እንደ ጎመን ቀቅሎ መብላትም ይቻላል። በአጠቃላይ እነዚህ ዕጽዋት እንደየ አካባቢው አጠራር ስማቸው ሊለያይ ይችላል።
የታሸጉ ምግቦችና ጦሳቸው
በፋብሪካ የተቀነባበሩና የታሸጉ፣ ጤናማ ያልሆኑ ምግቦች ወደ ሃገራችን በብዛት በመግባት ላይ ይገኛሉ ፣ እነዚህን ምግቦችና መጠጦች አዘውትሮ በመውሰድ የሚከሰቱ ተላላፊ ያልሆኑ ህመሞች እየጨመሩ ነው።በፋብሪካ የተቀነባበሩ ከፍተኛ ጨው፣ ስኳር፣ የሚረጋ ዘይትና የቅባት ይዘት ያላቸው ሃይል ሰጪ መጠጦችንና ምግቦችን አዘውትሮ መመገብ በጤና ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያስከትላል።
- ከልክ በላይ ለሆነ ውፍረት፣
- ካንሰር፣
- ልብ ህመም፣
- ስትሮክ፣
ዓይነት 2 የስኳር ህመም ያጋልጣሉ። የእነዚህ ጤናማ ያልሆኑ ምግቦችና መጠጦች ሰፊ አቅርቦት ወይም በገበያ ላይ እንደ ልብ መገኘትና ልቅ ማስታወቂያ በብዛት እንዲሸመቱ አድርጓቸዋል። ስለዚህ ለጤንነትዎ አስፈላጊውን ጥንቃቄ ያድርጉ፡፡
