የዩክሬኑ ፕሬዝዳንት ቮሎዲሚር ዘሌንስኪ ሀገራቸው ከሩሲያ ጋር የምታደርገውን ጦርነት ለመቋጨት የሰላም ስምምነቱ 90 በመቶ ዝግጁ ነው አሉ፡፡
ፕሬዝዳንቱ ይህን ያሉት የፈረንጆቹን 2026 አዲስ ዓመት አስመልከቶ ባስተላለፉት የእንኳን አደረሳችሁ መልእከት ነው፡፡
ዜሌንስኪ በመልእክታቸው፤ ለአራት ዓመታት ገደማ የዘለቀውን ጦርነት ለማስቆም በሁለቱ ሀገራት መካከል የሚደረገው የሰላም ስምምነት ድርድር 10 በመቶ ብቻ ይቀረዋል ብለዋል፡፡
የሰላም ስምምነቱ የቀጠናውን ሰላም ብሎም የዩክሬንን እና የአውሮፓን እጣ ፈንታ የሚወስን ነው ሲሉም ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።
ዩክሬን ሰላምን ለማስፈን ስትል ሁሉንም ማጣት ባትሻም ለሀገሪቱ ህልውና መቀጠል ጦርነቱን መቋጨት ያስፈልጋል ብለዋል።
የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን በበኩላቸው፤ የሩሲያን የማይበጠስ አንድነት፣ የጋራ መደጋገፍ እና የመጪ ግዜ ብሩህ ተስፋ አጠናክረን እንቀጥል ሲሉ ለህዝባቸው ባስተላለፉት የእንኳን አደረሳችሁ መልእከት ገልጸዋል።
የሩሲያን ጀግና ወታደሮች እናመሰግናለን ያሉት ፕሬዝዳንት ፑቲን፤ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሩሲያውያን በመንፈስ ከጎናቸው እንዲቆሙ ጥሪ ማቅረባቸውን ቢቢሲ ዘግቧል።
