በሀገር ውስጥ በስፋት የሚገኘውን የቀርከሃ (ሸንበቆ) ምርት ለወረቀት ግብዓትነት መጠቀም እንደሚገባ የኢትዮጵያ የደረጃዎች ኢንስቲትዩት ገልጿል፡፡
ወረቀት ከሚሰጠው ጠቀሜታ አንጻር ለወረቀት ግዢ ከፍተኛ ወጪ እንደሚወጣ፤ የኢንስቲትዩት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ይልማ መንግሥቱ ለአሐዱ ተናግረዋል።
በመጽሃፍ እና በህትመት ውጤቶች ላይ የዋጋ መናር እንዲከሰት ካደረጉ አበይት ምክንያቶች መካካል የወረቀት እጥረት ተጠቃሽ መሆኑን የገለጹት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፤ የወረቀት እጥረትን ለመፍታት እንደ መፍትሄ ከሚጠቀሱ ጉዳዮች መካከል አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን መጠቀም አንዱ መሆኑን አስረድተዋል።
“አክለውም እንደ ሀገር በስፋት የሚገኘውን የቀርከሃ ሸንበቆ ምርትን ለወረቀት ምርት በግብዓትነት መጠቀም ይገባል” ብለዋል።
ዋና ሥራ አስፈጻሚው በዚህ ዘርፍ ላይ ትኩረት ተሰቶት ሊሰራበት እንደሚገባ የገለጹ ሲሆን፤ በኢንስቲትዩቱ አማካኝነት የደረጃዎች ዝግጅት እንደሚከናወንም አብራርተዋል፡፡
አክለውም የጸደቁ ደረጃዎችን ተግባራዊ እንዲሆኑ ለማስቻል፤ ጉዳዩ የሚመለከታቸው ባላድርሻ አካላት ሚና ከፍተኛ በመሆኑ ኃላፊነትን መወጣት እንደሚገባ አሳስበዋል።
በሀገር ውስጥ አምራቾች እየተከናወነ የሚገኘውን የወረቀት ምርትን ማበረታታት፤ በዘርፉ ላይ የሚነሱ ክፍተቶችን ለመፍታት አስቻይ ሁኔታን እንደሚፈጥርም ጨምረው ተናግረዋል፡፡
በተጨማሪም በሀገር ውሰጥ ለወረቀት ምርት ግብዓትነት የሚውሉትን ለይቶ በማወቅ የምርት ሂደቱን ለመጨመር ጥረቶችን ማከናወን፣ እንደ አጠቃላይ በሕብረተሰቡ ዘንድ ያለውን ግንዛቤ ማጠናከር እንዲሁም ሁሉም ባላድርሻ አካላት በጋራ በመናበብ መስራት ተገቢ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
እ.ኤ.አ በ2018 የምስራቅ አፍሪካን የቀርከሃ ሀብት አስመልክቶ ይፋ በተደረገው ጥናት መሠረት፤ ኢትዮጵያ 1 ነጥብ 47 ሚሊዮን ሄክታር የቀርከሃ ሀብት እንዳላት ተገልጿል፡፡
(አሐዱ ሬዲዮ)
