የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ግንቦት 6 ቀን 2017 ዓ.ም በተደረገ ስብሰባ የዘንድሮ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በርካታ ሥር ነቀል ለውጦችን ማምጣት የሚችል ፤ ለነገይቱ የቤተክርስቲያን ተረካቢ ወጣቶች መሰረት የጣለ እንዲሆን ያለመ ምክረ ሐሳብ ተወያይቶ ማቅረቡን አስታውቋል።
ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ቀርበው መፍትሔ እንዲሰጥባቸው ከቀረቡት ውስጥ ፦ የቤተክርስቲያንን ሲኖዶሳዊ ልዕልና እና አንድነትን ማስጠበቅ ፣ የቤተክርስቲያንን አስተዳደራዊ ችግሮችን በመለየት መፍታት ፣ የሥነ ምግባር ግድፈት እና የቀኖና ጥሰት መበራከት ፣ በሀገራዊና ዓለም አቀፍ ጉዳይ ላይ የሚኖሩ ተሳትፎዎች ዋና ዋና ጉዳዮች ስለመሆናቸው በመልእክቱ ተላልፏል።
ሐሰተኛ የሆኑ የኑፋቄ ትምህርቶች ፣ በሰላም እጦት የሚገኙ አህጉረ ስብከቶች ፣ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ሚና ፣የሀብት ብክነት ፣ ዘመኑን የዋጀ የአሠራር መንገድ መዘርጋት ፣ መንፈሳዊ አገልግሎት ላይ የሚስተዋሉ እና አፈንግጠው የወጡ ሥርዓቶች ፣ በከተማ ልማት መስፋፋት የምእመናን ከአምልኮ ሥፍራ መራቅ ፣ ሀገራዊ የችግር አፈታት መንገዶች ላይ ምልዓተ ጉባኤውም በስፋት እንዲወያይ አንድነቱ በዝርዝር ካስቀመጣቸው ሐሳቦች መሐል ይገኙበታል።
እነዚህን እና ሌሎች የውይይት ሐሳቦችን በዝርዝር በማቅረብ ” የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ መፍትሔ በመስጠት ሐዋርያዊ አደራውን እንዲወጣ በልጅነት መንፈስ ዝቅ ብለን እንማፀናለን! ” በማለት አንድነቱ መልእክቱን አጋርቷል።
