አዲሱን የኢራን መንፈሳዊ መሪ ለመያዝ ዩናይትድ ስቴትስ ከፍተኛ ወሮታ እንደምትከፍል ገለፀች። የሟቹ አያቶላህ አሊ ኻመኔይ ልጅ ሞጅታባ ኻመኔይ እና ሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናት የት እንዳሉ መረጃ ለጠቆመ እስከ አስር ሚሊዮን ዶላር እንደሚከፈል ዋሽንግተን ዲሲ የሚገኘው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።
ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ በኢንተርኔት ባሰራጨው ማስታወቂያ ከኻመኔይን በተጨማሪ የሀገር ውስጥ ሚኒስትሩን፣ የኢራን ብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት ዋና ፀሐፊ እና የስለላ ሚኒስትሩን በጠቅላላ 10 ከፍተኛ ባለስልጣናትን እያፈላለገ ይገኛል።
የ56 ዓመቱ ሞጅታባ ኻመኔይ የአባታቸውን ቦታ ከተረከቡ ጊዜ አንስቶ በመገናኛ ብዙኃን ቀርበው አያውቁም። እንደ ዩናይትድ ስቴትስ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሮቢዮ እና መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት ከሆነ ኻመኔይን ጉዳት ሳይደርስባቸው አልቀረም። ይህ ግን በየትኛውም ወገን አልተረጋገጠም።
