በዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ከእስራኤል ጋር የቀረበው የተኩስ አቁም የስምምነት ሀሳብ በሃማስ በኩል አሁን ላይ ውይይት እየየደረገበት ቢሆንም አሁን ባለው መልኩ ግን በጋዛ “ግድያ እና ረሃብ እንዲቀጥል” ብቻ እንደሚያደርግ የፍልስጤሙ ቡድን ባለስልጣናት ተናግረዋል። የዋይት ሀውስ የፕሬስ ሴክሬታሪ ካሮሊን ሌቪት በሰጠት መግለጫ እንደተናገሩት እስራኤል በተኩስ አቁም ሀሳብ ላይ “ፈርማለች” እናም የትራምፕ አስተዳደር የመካከለኛው ምስራቅ መልዕክተኛ ስቲቭ ዊትኮፍ ሀሳቡን ሃማስ ከግምት ውስጥ እንዲያስገባ አቅርበዋል ብላለች።
የሃማስ የፖለቲካ ቢሮ አባል ባሴም ናይም ለሮይተርስ የዜና ወኪል እንደተናገሩት ስምምነቱ የትኛውንም የህዝባችንን ጥያቄ አያሟላም፤ ግንባር ቀደሙ መሆን ያለበት ጦርነቱን ማቆም ነው ብለዋል። ይሁን እንጂ የንቅናቄው አመራር ለሐሳቡ የሚሰጠውን ምላሽ ከሙሉ አገራዊ ኃላፊነት ጋር እያጠና ነው ሲሉ ናኢም አክለዋል። ሃማስ አርብ ወይም ቅዳሜ ምላሽ ይሰጣል ሲል የፍልስጤም ቡድን ምንጭ ለሮይተርስ ተናግሯል። የአዲሱ ሀሳብ ዝርዝር ለህዝብ ይፋ አልተደረገም ነገር ግን የሃማስ ከፍተኛ ባለስልጣን ሳሚ አቡ ዙህሪ ለሮይተርስ እንደተናገሩት በወሳኝ መልኩ እስራኤል በጋዛ ላይ የምታደርገውን ጦርነት ለማስቆም፣ የእስራኤል ወታደሮችን ከቀዬው ለማስወጣት ወይም ዕርዳታ ወደ ጦርነት ወደማታመሰው ግዛት እንድትገባ የገባችውን ቃል አልያዘም ሲሉ ተደምጠዋል።
ረቂቅ ቅጂን ጠቅሶ ሮይተርስ ሃሳቡ የ60 ቀናት የተኩስ አቁም ስምምነትን ይዘረዝራል ብሏል። ሃያ ስምንት የእስራኤል ታጋቾች በህይወት ያሉ እና የሞቱትን አስክሬናቸው ከእገታ ነፃ እንዲሆን ያትታል። 1,236 ፍልስጤማውያን እስረኞችን እና 180 የሞቱ ፍልስጤማውያንን አስከሬን ለመለቀቅ በመጀመሪያው ሳምንት እንዲችሉ የተኩስ አቁም ስምምነቱ ላይ ቀርቧል። በፕሬዚዳንት ትራምፕ እና በአደራዳሪዎቹ ግብፅ እና ኳታር ዋስትና ተሰጥቶታል የተባለው ይህ እቅድ ሃማስ እንደፈረመ ርዳታ ወደ ጋዛ እንደሚላክም ተመላክቷል። የእስራኤል መንግስት የቅርብ ጊዜውን የተኩስ አቁም ስምምነት ሀሳብ ማፅደቁን ግን በይፋ አላረጋገጠም።
