በኢትዮጵያ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ከአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አባል ቲዬሪ ማሪያኒ ጋር በሀገራዊና ቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ ውጤታማ ውይይት አካሂዷል።
የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ዶ/ር ዲማ ኖጎ ኢትዮጵያ በታሪክ አጋጣሚ የባህር በር ማጣቷን አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት ሀገሪቱ እያስመዘገበችው ካለው የኢኮኖሚና የሕዝብ ቁጥር ዕድገት አንጻር የራሷ የባህር በር መኖሩ ለህልውናዋ ወሳኝ መሆኑን አብራርተዋል። ኢትዮጵያ ይህንን ጥያቄ በሰላማዊ መንገድና በስምምነት ለመፍታት ቁርጠኛ መሆኗንም አረጋግጠዋል።
የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አባሉ ቲዬሪ ማሪያኒ በበኩላቸው፣ የኢትዮጵያ የባህር በር የማግኘት ፍላጎት ወቅታዊ፣ ታሪካዊና በጠንካራ ምክንያት ላይ የተመሰረተ መሆኑን ገልጸዋል።
ጥያቄው ተገቢ መሆኑንና ለቀጠናው የጋራ ዕድገት ያለውን የጎላ ፋይዳ ያስረዱት ማሪያኒ፣ እ.ኤ.አ በ1950ዎቹ በተባበሩት መንግሥታት የነበረውን የታሪክ ሂደት በመጥቀስ የኢትዮጵያን ፍላጎት ለማሳካት አስፈላጊውን ዲፕሎማሲያዊ ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውን በይፋ አስታውቀዋል።
በተጨማሪም በውይይቱ ወቅት የታላቁ የህዳሴ ግድብ በታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ላይ ምንም ዓይነት የውኃ መቀነስ አለማስከተሉ በተግባር መረጋገጡ ተነስቷል።
መንግሥት 7ኛው ሀገራዊ ምርጫ ያለምንም ችግር እንዲጠናቀቅ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ዶ/ር ዲማ ኖጎ ያብራሩ ሲሆን፣ መድረኩ በአውሮፓ ህብረት፣ በፈረንሳይና በኢትዮጵያ ፓርላማዎች መካከል ያለውን ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር ያለመ መሆኑ ተመላክቷል።
