የተባበሩት መንግስታት የዓለም ምግብ ፕሮግራም (WFP) በኢትዮጵያ ለሚያደርገው የሰብአዊ እርዳታ አቅርቦት በአስቸኳይ 228 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር የገንዘብ እጥረት እንዳጋጠመዉ ይፋ አደረገ።
ይህ የገንዘብ እጥረት ከመጋቢት እስከ ነሐሴ 2017 ዓ.ም. ያለውን ጊዜ የሚሸፍን ሲሆን ቀድሞውንም የምግብ ርዳታ እየተቀነሰ ባለበት ወቅት ላይ የከፋ ችግር ሊያስከትል እንደሚችል አስጠንቅቋል።
ድርጅቱ ባወጣው ሪፖርት እንዳመለከተው በከፍተኛ የገንዘብ እጥረት ምክንያት የእርዳታ ምግቡን ወደ 65 በመቶ ዝቅ ለማድረግ ተገዷል።
ከዚህም በላይ ለተመጣጠነ ምግብ እና ለስደተኞች የሚሰጠው እርዳታ አቅርቦት መስመር ሊቋረጥ መቃረቡ በአሁኑ ወቅት ባለው ሰብአዊ ቀውስ ላይ ከፍተኛ ጫና እየፈጠረ መሆኑን አስረድተዋል።
በተጨማሪም በክልሉ ያለው የፀጥታ ሁኔታ እየተባባሰ መምጣቱ የርዳታ አቅርቦቱን እያስተጓጎለ ነው። በተለይም በአማራ እና በኦሮሚያ ክልሎች የታጠቁ ኃይሎች የሚነሱ ግጭቶች፣ በአጃቢዎች ላይ የሚደርሱ ጥቃቶች እና አፈናዎች እየጨመሩ መምጣቱን አስታውቋል።
በሌላ በኩል በትግራይ ያለው ውጥረት እንዲሁም ከኤርትራ ጋር ያለው ሁኔታ እየተካረረ መምጣቱ እና በሶማሌ ክልል ደግሞ በርካታ የአል-ሻባብ እና አይሲስ ታጣቂዎች ተጠርጥረው መታሰራቸው ቀጣይነት ያለው የፀጥታ ችግር እና የሽብርተኝነት ስጋት መኖሩን በሪፖርቱ ገልጿል።
የዓለም ምግብ ፕሮግራም ይህንን አስቸኳይ የገንዘብ እጥረት ለመቅረፍ እና በችግር ላይ ያሉ ዜጎችን ለመርዳት ዓለም አቀፍ ለጋሽ አካላት ፈጣን ምላሽ እንዲሰጡ ጥሪ አቅርቧል።
ካፒታል
