አገራቸውን በልዩ ልዩ መንገድ ፣በተለይም ከዕውቀትና ከዕድገት ጋር በተያያዘ ያገለገሉት ዶክተር ያየህይራድ ቅጣው የሕይወት ታሪካቸውን ፅፋው ሊያስነብቡና ሊያስመርቁ እንደሆነ ተሰማ። ዶክተር በአሁኑ ሰዓት የ85 ዓመት ሰው ሲሆኑ ለአገራቸውም ከፍተኛ ፍቅር እንዳላቸው ይነገርላቸዋል።
“ከእናት እቅፍ እስከ ልጅ ልጅ ምርኲዝ ትዝታዎቼ ” የሚል ርዕስ የተሰጠው ይህ መፅሐፍ 350 ገፆች አሉት፡፡ የመፅሐፍ ዝግጅቱን እና ምረቃውን የሚያከናውነው ተወዳጅ ሚድያ እና ኮምዩኒኬሽን ( ዕዝራ እጅጉ) ሲሆን አርትኦቱም በናይእግዚ ኅሩይ ተሠርቷል።
በዕለቱ በዶክተር ያየህይራድ ቅጣው ላይ ያተኮረ የ3 ሰዓት የድምፅ ዶክመንተሪ በይፋ የሚመረቅ ሲሆን ሳቤህ ዞንና ተወዳጅ ሚድያ በትብብር እንዳሰናዱት ለማወቅ ተችሏል።
ዶክተር ያየህይራድ ቅጣው ከጄነራል ዊንጌት ብርቱ ተማሪዎች አንዱ የነበሩ ሲሆን በፈረንሳይ አገርም የህክምና ትምህርታቸውን ለመከታተል የቻሉ ናቸው፡፡
የዕድገት በሕብረት ዘመቻ ላይ የማይዘነጋ አሻራ ያኖሩት ዶክተር ያየህይራድ ቅጣው፣በትምህርት ሚኒስትርነት እናት አገራቸውን በትጋት ያገለገሉ ናቸው፡፡
የዶክተር ያየህይራድ ባለቤትና ልጆች ፣ለዚህ መፅሐፍ ትልቅ ትብብር ያሳዩ ሲሆን መፅሐፉም ታላላቅ ኢትዮጵያዊያን በሚታደሙበት ጥር 9 2018 በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መኮንን አዳራሽ እንደሚመረቅ ታውቋል።
የመፅሐፉን የአርትዖት ሥራ 5 ወር የወሰደ ሲሆን አጠቃላይ የመፅሀፉ ፕሮጀክት 8 ወራትን መውሰዱን የስነዳ ሥራው አስተባባሪ ዕዝራ እጅጉ ተናግሯል። የምረቃ መርሀ- ግብሩ ላይ ታላላቅ እንግዶች የሚታደሙ ሲሆን ደመላሽ አማረ የመፅሀፍ ቅኝት ያቀርባል። የዶክተር ያየህይራድ ቅጣው ወዳጅ የሆኑት ፕሮፌሰር ሽብሩ ተድላ ከተናጋሪዎች መካከል አንዱ ናቸው።
ሳምራዊት አዘነ እና ዕንቁ ዜማዎች ታዳሚውን ዘና እንደሚያደርጉት ለማወቅ ተችሏል። የዚህ መፅሀፍ የአርትዖት አስተባባሪ እና ሁነት አዘጋጅ ዕዝራ እጅጉ 21 መፅሀፍትን እስከዛሬ ሠርቶ ያስነበበ ሲሆን የ45 ሰዎችንም ታሪክ በሲዲ አሳትሟል። በተጨማሪም የአማርኛ ኢንሳይክሎፒዲያንም ለሕትመት ማብቃት የቻለ። ወደ 40 የሚጠጉ ሁነቶችንም ዕውን ማድረግ የቻለ ነው።
