የዛሬው የፎረሙ መክፈቻ በባሕር ዳር ከተማ ውስጥ ተካሂዷል። ቀጣይ የፎረሙ መርሐ ግብሮችም በአዲስ አበባ ከተማ የሚካሄዱ ይኾናል።
በባሕር ዳር ከተማ የነበረውን ቆይታ አስመልክተው መግለጫ የሰጡት የአማራ ክልል ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ ኮሚሽነር ዘላለም መንግሥቴ (ዶ.ር) የ11ኛው የጣና ፎረም የባሕር ዳር ከተማ ቆይታ በስኬት ተጠናቅቋል ብለዋል።
የባሕር ዳር ከተማ ልዩ ምልክት በኾነው ጣና ፎረም ለመሳተፍ የሚመጡ እንግዶችን ከዋዜማው ጀምሮ በመቀበል በከተማዋ ውስጥ የሰመረ ቆይታ እንዲኖራቸው ለማስቻል የጸጥታ የጋራ ግብረ ኀይል ተቋቁሞ በቂ ዝግጅት ተደርጎ እንደነበር ተናግረዋል።
ይህም እንግዶች ከፎረሙ ጎን ለጎን ባሕር ዳር ከተማን እና በጣና ሐይቅ ላይ የተሠሩ ልማቶችን ተዘዋውረው እንዲያዩ እና ያማረ ቆይታ እንዲኖራቸው አስችሏል ነው ያሉት።
እንግዳ ወዳዱ የባሕር ዳር ሕዝብም እንግዶቹን ተቀብሎ እሴቱን በጠበቀ መልኩ አስተናግዷል፤ ምሥጋናም ይገባዋል ብለዋል።
የጣና ፎረም ስኬት ባሕር ዳር ከተማ ያካበተችውን ዓለም አቀፍ መድረኮችን የማዘጋጀት ብቃት ያስመሰከረ እንደኾነም ተናግረዋል።
በቀጣይም እንዲህ ዓይነት ዓለም አቀፍ፣ አሕጉራዊ እና ሀገር አቀፍ ጉባኤዎች በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች ማካሄድ ቢፈለግ አስተማማኝ የማስተናገድ አቅም አለ ነው ያሉት።
ለጣና ፎረም ሥኬት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ያደረጉ አካላትን በሙሉ አመሥግነዋል።
