የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር) ማክሰኞ ጥር 26 ቀን 2018 ዓ.ም የመንግሥትን የ2018 በጀት ዓመት የ6 ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያቀርባሉ፡፡
በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት አንቀፅ 55 ንዑስ አንቀፅ (17) እና በምክር ቤቱ የአሠራርና የአባላት የሥነ- ምግባር ደንብ ቁጥር 6/2008 አንቀፅ 81 ንዑስ አንቀፅ (1 እና 3) መሠረት የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጠቅላይ ሚኒስትሩን እና ሌሎች የፌዴራሉ መንግሥት ባለስልጣናትን ለጥያቄ የመጥራትና የሕግ አስፈፃሚውን አካል አሠራር የመመርመር፣ የመከታተልና የመቆጣጠር ሥልጣን አለው፡፡
በዚሁ ሕገ መንግሥታዊና የምክር ቤቱ የአሠራርና የአባላት ሥነ-ምግባር ደንብ መሰረት 6ኛው የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመኑ ማክሰኞ ጥር 26 ቀን፣ 2018 ዓ.ም በሚያካሂደው 10ኛ መደበኛ ስብሰባው የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር)በምክር ቤቱ ተገኝተው የመንግሥትን የ2018 በጀት ዓመት የ6 ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት የሚያቀርቡና ከምክር ቤቱ አባላት ለሚነሱ ጥያቄዎችም ማብራሪያና ምላሽ እንደሚሰጡ ይጠበቃል፡፡
በጉባኤው ላይ ጥሪ የተደረገላቸው ተጋባዥ እንግዶች፣ የተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮችና የዓለም አቀፍ ተቋማት ተጠሪዎች፣ የሐይማኖት አባቶች፣ ታዋቂ ግለሰቦችና የተፎካካሪ ፓርቲ አመራሮች የሚገኙ ሲሆን የጉባኤው ሙሉ ሂደትም ከጠዋቱ 2፡30 ጀምሮ በቀጥታ ሥርጭት የሚተላለፍ ይሆናል፡፡
