ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከመላው ሀገሪቱ ከተውጣጡ የንግዱ ማህበረሰብ ተወካዮች ጋር ባደረጉት ውይይት ከተሳታፊዎች ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
በመድረኩ ህገወጥ የንግድ ስርዓቶች፣ የንብረት ታክስ፣ ሰላምና ደህንነት እንዲሁም ከሙስና ጋር የተያያዙ የንግዱ ዘርፍ እንቅፋት የሆኑ ጉዳዮች ከንግዱ ማህበረሰብ በኩል ተነስተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሰጡት ምላሽና ማብራሪያ፤ እየተነሱ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት በጋራ መስራት ይገባል ብለዋል።
ዲጂታል አገልግሎትን ማጠናከር የሌብነት በር የሚዘጋ በመሆኑ በቀጣይ በትኩረት እንደሚሰራበትም ተናግረዋል።
ሌብነትን በተመለከተ በመረጃ የተደገፈ ጥቆማ የሚቀርብ ከሆነ የትኛውም አመራር ተጠያቂ ይሆናል ብለዋል።
ህገወጥ የኮቴ ክፍያዎችን ለማስቀረት ክፍያ የሌለበት ፍተሻ የተጠናከረበት የኬላ ቁጥጥር ስርዓት እንዘረጋለን ሲሉም ተናግረዋል።
የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች በኢንዱስትሪ የመስክ ልምምድ የማድረግ ግዴታ እንደሚጣልባቸና ይህም ነባራዊ ሁኔታን የተረዳ ገበያውን የሚመጥን የሰው ሀይል ለማፍራት እንደሚያስችል ገልፀዋል።
በዲፕሎማሲ መስክም የንግዱ ማህበረሰብ ተጠቃሚ የሚሆንባቸው የግንኙነት መስመሮች መዘርጋታቸውን ጠቁመዋል።
ለውጥ ለማምጣት መራር ወቅቶችን ማለፍ የግድ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፤ የጋራ ርዕይ ካለን እንወጣዋለን ሲሉ ገልጸዋል።
