ለሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ 51 ሺህ የምርጫ ጣቢያዎች መዘጋጀታቸውን የኢትዮጵያ ሲቪል ማኅበራት ድርጅቶች ጥምረት አስታውቋል።
የምርጫ ታዛቢ ድርጅቶች ጥምረት ዋና ዳይሬክተር አቶ አበራ ኃይለማርያም እንደገለጹት፤ ምርጫውን ለመታዘብ 5 ሺህ ታዛቢዎችን ለማሰማራት የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ተጠናቀዋል።
ከእነዚህም መካከል 522 የሚሆኑት የረዥም ጊዜ ታዛቢዎች ሲሆኑ፣ የምርጫ ጣቢያዎችን የመጎብኘትና የመራጮች ምዝገባ ሂደቱን የመታዘብ ኃላፊነት ተሰጥቷቸዋል።
ታዛቢዎቹ በወረቀት የሚከናወኑ 12 የመራጮች ምዝገባ ጣቢያዎችን እንዲሁም በታብሌት የሚከናወኑ 8 የምዝገባ ጣቢያዎችን በቅርበት እንደሚከታተሉ ዳይሬክተሩ ገልጸዋል።
የታዛቢዎቹ የክትትል ሥራ እስከ ሚያዝያ 14 ቀን 2018 ዓ.ም. ድረስ የሚቀጥል ሲሆን፣ በምርጫው ዕለትም ሂደቱን በንቃት እንደሚታዘቡ ታውቋል። ይህም የምርጫውን ተዓማኒነትና ግልጽነት ለማረጋገጥ ዓይነተኛ ሚና ይኖረዋል ተብሏል።
የታዛቢዎችን አቅምና ጥራት ለማረጋገጥ “ዲጂታል ኤሌክሽን ኦብዘርቬሽን ወርክ ስፔስ” የተባለ አዲስ የቴክኖሎጂ ሥርዓት ስራ ላይ መዋሉን አቶ አበራ ጠቁመዋል።
ይህ ቴክኖሎጂ ቀደም ሲል ይስተዋሉ የነበሩ የታዛቢዎች ምልመላና የቁጥጥር ችግሮች ለመፍታት እንዲሁም የጊዜ ብክነትን ለመቀነስ የሚያስችል ነው ተብሏል።
አዲሱ አሠራር በቀጣዩ ጠቅላላ ምርጫ የታዛቢዎችን የሥራ አፈጻጸም በብቃት ለመቆጣጠር እንደሚያስችል ጥምረቱ ገልጿል።
ለአሐዱ ራዲዮ
