ኢትዮጵያ በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ የዓለም አቀፍ አትሌቲክስ ውድድርን በአዲስ አበባ ለማዘጋጀት የሚያስችላትን ዕድል ማግኘቷን የከተማዋ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ይፋ አደረጉ።
በዓለም አትሌቲክስ የውድድር ካላንደር ውስጥ በይፋ የተካተተውና “One Day Meeting” የተሰኘው ይህ ታላቅ ውድድር፣ በፈረንጆቹ አቆጣጠር ሚያዝያ 18 ቀን 2026 በአዲስ አበባ የሚከናወን ይሆናል።
ከንቲባዋ ይህንን ታሪካዊ ድል አስመልክተው ባስተላለፉት የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት፤ ስኬቱ በከተማዋ ሲከናወኑ የቆዩ ዓለም አቀፍ ግንኙነቶች፣ የስፖርት ዲፕሎማሲ እና የመሠረተ ልማት መስፋፋት ሥራዎች ውጤት መሆኑን ገልጸዋል።
የዓለም አትሌቲክስ ውድድር ዋና ዳይሬክተር ፒርስ ኦክላጋን በኢትዮጵያ ባደረጉት ጉብኝት አገሪቱ ያላትን በቂ የማዘጋጀት አቅም መመስከራቸውን ተከትሎ የተመዘገበው ይህ ስኬት፣ ለኢትዮጵያ አዲስ ምዕራፍ እንደሚከፍት ታምኖበታል።
በዓለም አቀፍ ባለሙያዎች የሚመራው ይህ ውድድር ለአገር ውስጥ ሙያተኞች የልምድ ልውውጥ ከመፍጠሩ ባለፈ፣ ለሚሳተፉ አትሌቶችም ከፍተኛ ሽልማት የሚያበረክት ነው።
ከንቲባዋ ለዚህ ውጤት መመዝገብ የላቀ ሚና ለተጫወቱት የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር፣ ለኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽንና ለሌሎች ባለድርሻ አካላት ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
ውድድሩ ኢትዮጵያ የአትሌቲክስ መገኛነቷን ለዓለም የምታሳይበትና የስፖርት ዲፕሎማሲዋን ወደ ላቀ ከፍታ የምታደርስበት መድረክ እንደሚሆንም ይጠበቃል።
