በኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን በሚገኙ የተለያዩ ወረዳዎች ውስጥ በንጹሃን ዜጎች ላይ እየተፈጸመ ያለው ግድያ፣ እገታና መፈናቀል በአሳሳቢ ሁኔታ መቀጠሉን የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) አስታወቀ።
ኮሚሽኑ ባወጣው መግለጫ መሠረት፣ በተለይም ከጥቅምት 2018 ዓ.ም. ጀምሮ በሽርካ፣ በጉና፣ በመርቲ እና በሌሎች የአርሲ ዞን አካባቢዎች የታጠቁ ኃይሎች በሰነዘሩት ተደጋጋሚ ጥቃት ሳቢያ የሰው ሕይወት መጥፋቱን፣ የአካል ጉዳት መድረሱንና መጠነ ሰፊ የንብረት ውድመት መከሰቱን ገልጿል።
የግጭቱ መባባስ በሺዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎችን ለስደት የዳረገ ሲሆን፣ የካቲት 19 ቀን በሽርካ እና ሮቤ ወረዳዎች በንጹሃን ላይ የተፈጸመው ግድያና እገታ የችግሩን አስከፊነት አጉልቶ አሳይቷል።
የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ መንግሥት የዜጎችን ደህንነት የማስከበር ሕገ-መንግሥታዊ ግዴታውን እንዲወጣና በአካባቢው በቂ የጸጥታ ኃይል እንዲያሰማራ ጥሪ አቅርበዋል።
