“ቡድኑ ትግራይን ለማተራመስና ኢትዮጵያን
ለመውጋት ከኤርትራ መንግስት ጋር እየሰራ ነው”
በቀድሞው የህወኃት አመራሮች የተመሰረተው ዴሞክራሲያዊ ስምረት ትግራይ (ስምረት) ፓርቲ፤ መንግሥት በምርጫ ቦርድ የተሰረዘው ‘ህወሓት’ ላይ ህጋዊ እርምጃ መውሰድ እንጂ ማስታመም አይገባውም አለ፡፡
ስምረት ፓርቲ ባወጣው መግለጫ፤ “ህወሓት ትግራይን ለማተራመስና ኢትዮጵያ ለመውጋት ከኤርትራ መንግስት እየሰራ ነው” ሲል ወንጅሎታል፡፡
“ከአሁን በኋላ በትግራይ ላይ የሚፈፀሙ ጥፋቶች ብቸኛው ተጠያቂ ከዓለም አቀፍና አገራዊ ህጎች የተቃረነው ወመኔው ኋላ ቀር ቡድንና መሰሎቹ መሆናቸውን የኢትዮጵያ መንግሥት መገንዘብ አለበት” ብሏል ፓርቲው፡፡
ለህዝቡ ባስተላለፈው መልዕክትም፤ “የሃይማኖት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ ወጣቶች፣ በአገር ውስጥና በመላ ዓለም የምትገኙ ትግራዋዮች፤ ቡድኑ በስልጣን ላይ የሚቆይባቸው እያንዳንዱ ቀናት በህዝብ ላይ አስከፊ መከራና ስቃይ የሚያስከትሉ መሆናቸውን በመረዳት ትግላችሁን አጠናክሩ” ሲል ጥሪ አቅርቧል።
ፓርቲው ለታጠቀው ሰራዊት ባስተላለፈው ጥሪ፤ “ሌት ተቀን የጦርነት ነጋሪት ከሚጎስመው ኋላ ቀር ቡድን ራሳችሁን በማራቅ ከሰላም ፈላጊ ህዝብ ጎን ተሰለፉ” ብሏል።
“ከአሁን በኋላ በትግራይ ህዝብ ላይ የሚፈፀም ወንጀልንም ይሁን የሚቀሰቀስ ጦርነትን በዝምታ ማየት በህዝብ ላይ የሚያስከትለውን ከባድ አደጋ መዘንጋት ነው” ያለው ስምረት ፓርቲ፤ “አደጋውን አስቀድሞ ለማስቀረት ሁሉም የሚመለከታቸው አካላት ሚናቸው ከወዲሁ እንዲወጡ” ለአገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ተቋማት ጥሪውን አቅርቧል።
