ማኅበሩ በምሥራቅ ወለጋ ሀገረ ስብከት በነቀምት ምስካበ ቅዱሳን ዑራኤል ወሳሙኤል አንድነት ገዳም ያስገነባው አዳሪ አብነት ትምህርት ቤት በዛሬው ዕለት በብፁዕ አቡነ ሩፋኤል የጋምቤላ ክልልና የደቡብ ሱዳን ፣የቤንሻንጉል ጉሙዝ አሶሳ፣የቄለም ወለጋ፣የምዕራብ ወለጋ፣የምሥራቅ ወለጋ፣የሆሮ ጉዱሩ ወለጋ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተመርቋል፡፡
የአዳሪ አብነት ትምሕርት ቤቱ በተመላላሽ የሚማሩትን ጨምሮ 60 ደቀ መዛሙርትን ተቀብሎ የሚያስተናግድ ሲሆን የ 2 መምህራን እና የ 32 ተማሪዎች ማደሪያ ከሙሉ ግብዓቱ፣ የመማሪያ ጉባኤ ቤት፣ መመገቢያ አዳራሽ፣ ማብሰያ ቤት፣ የልብስ ማጠቢያ ገንዳዎችና እና መጸዳጃ ቤቶችን ያካተተ መሆኑ ተነግሯል።
በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ሩፋኤል አዳሪ አብነት ት/ቤቱ ከዛሬ ጀምሮ ተማሪ ተቀብሎ ለማስተማር ዝግጁ መሆኑን ፤ እንዲሁም ከአራቱም ወለጋዎች ተማሪዎች ገብተው እንዲማሩ እንደሚሠሩ እና ከቅዱስ ሲኖዶስ በጀት እንደሚያስፈቅዱ ተናግረዋል፡፡
ታኅሣሥ ወር 2016 ዓ.ም ተጀምሮ በአንድ ዓመት የተጠናቀቀው የትምህርት ቤቱ ግንባታ ፕሮጀክት 8,870,407.125 (ስምንት ሚሊዮን ስምንት መቶ ሰባ ሺህ አራት መቶ ሰባት ብር ከ3/100 ሳንቲም) ብር ወጪ የወጣበት ሲሆን በሀገር ውስጥ እና ከሀገር ውጪ የሚገኙ በበጎ አድራጊ ምዕመናን ድጋፍ አድርገዋል፡፡
ይህ የአዳሪ አብነት ትምህርት ቤት በሀገረ ስብከቱ እና አጎራባች አህጉረ ስብከት የሚታየውን የአገልጋይ አጥረት ችግር እንደሚፈታ ታምኖበት የተተገበረ ፕሮጀክት መሆኑም ተዘግቧል።
