የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ፣ የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የሥራ ዘመን ለቀጣይ ስምንት ወራት እንዲራዘም በሙሉ ድምፅ አፅድቋል።
የውሳኔ ሃሳቡን ለምክር ቤቱ አባላት ያቀረቡት የዲሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ እውነቱ አለን፤ ኮሚሽኑ እስካሁን ከትግራይ ክልል በስተቀር በአስራ አንድ ክልሎችና በሁለቱ ከተማ መስተዳድሮች አጀንዳ ማሰባሰቡን አስታውቀዋል።
ኮሚሽኑ ለብሔራዊ ጉባኤው ተሳታፊዎችን የመለየት፣ አወያዮችን የመመልመል እና የአጀንዳ ቀረፃ ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን በመጥቀስ፤ በቀጣይ የትግራይ ክልልን በማካተት ሥራውን ማጠናቀቅ እንዲችል ተጨማሪ ስምንት ወራት ቢሰጠው የተሻለ መሆኑን በውሳኔ ሃሳባቸው ጠይቀዋል።
የምክር ቤቱ አባላትም ኮሚሽኑ ቀሪ ሥራዎቹን እንዲያጠናቅቅ በማመላከት የውሳኔ ሃሳቡን ደግፈዋል። በዚህም መሠረት የኮሚሽኑ የቆይታ ጊዜ ከየካቲት 15 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ለሚቆጠሩ 8 ወራት እንዲራዘም ውሳኔው ጸድቋል።
