የኢትዮጵያን ሀገር በቀል ዕውቀቶች ለይቶ ለማጥናትና በሥርዓት እንዲሰነዱ ለማድረግ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ሰፊ የምርምር ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ትምህርት ሚኒስቴር ገልጾአል።
በትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርት ልማት ዘርፍ የምርምርና የማኅበረሰብ መሪ ሥራ አስፈጻሚ ዶክተር ሰራዊት ሐምዲሶ እንደተናገሩት፣ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚገኙ ጥንታዊና ጠቃሚ ዕውቀቶች ተለይተው ለትውልድ እንዲተላለፉና ለልማት እንዲውሉ ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል።
በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሚከናወኑ እነዚህ ጥናትና ምርምሮች የማኅበረሰቡን ችግሮች በመፍታትና ባህላዊ እሴቶችን በማሳደግ ረገድ ከፍተኛ ሚና እንዳላቸው ተገልጿል። ሀገር በቀል ዕውቀቶችን በመለየት ለመሰነድ ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር ዩኒቨርሲቲዎች የሚሰጡት የጥናትና ምርምር ግብዓት ወሳኝ መሆኑን ዶክተር ሰራዊት አጽንኦት ሰጥተውበታል።
በአሁኑ ወቅት በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚገኙ ከ40 በላይ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ከመማር ማስተማር ሥራቸው በተጨማሪ፣ ችግር ፈቺ የሆኑ ጥናትና ምርምሮችን በማከናወን ላይ ይገኛሉ።
የዘርፉ መሪ ሥራ አስፈጻሚው አክለውም፣ ሀገር በቀል ዕውቀቶች በሳይንሳዊ መንገድ ተጠንተው ለእውቀትና ለመረጃ ግብዓትነት እንዲውሉ አቅጣጫ ተቀምጦ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
ይህም የሀገርን ተወዳዳሪነትና የውስጥ አቅምን ለማሳደግ ትልቅ ፋይዳ እንደሚኖረው ታምኖበታል።
