በርካታ የኪየቭ ወረዳዎችን በመምታት አንድ አፓርትመንት ባፈረሰ የሩስያ ሰው አልባ አውሮፕላኖች እና የሚሳኤሎች ጥቃት ቢያንስ ስድስት ሰዎች ሲገደሉ ከ50 በላይ ቆስለዋል ሲሉ የዩክሬን ባለስልጣናት ተናግረዋል።
ከሟቾቹ መካከል አንዱ የስድስት አመት ህጻን ሲሆን የኪየቭ ወታደራዊ አስተዳደር ሃላፊ ቲሙር ታኬንኮ የሟቾች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል እና ከሁለት ደርዘን በላይ በሆኑ ቦታዎች ላይ ጉዳት መድረሱን ተናግረዋል።
ከፍተኛ ድምፅ ያለው የሩሲያ ሰው አልባ አውሮፕላኖች በመዲናዋ ላይ ለሰዓታት ሲሰሙ ነበር።
የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ቭላድሚር ፑቲን የተኩስ አቁም ስምምነት እስከ ኦገስት 8 ድረስ ካልተስማሙ ጠንከር ያለ ማዕቀብ በሞስኮ ላይ ለመጣል ቢያስፈራሩም የሩሲያ ጥቃቶች ግን አሁንም ተጠናክረው ቀጥለዋል።
የዩክሬን አየር ሃይል እንዳለው ሩሲያ 309 ሰው አልባ አውሮፕላኖችን እና ክራይዝ ሚሳኤሎችን መተኮሷን እና የአየር መከላከያ ሰራዊት ከመጣው የተወሰኑትን ቢጠልፍም በርካታ የተኩስ እሩምታ ደርሷል ብሏል።
ከጥቃቱ አንዱ የመኖሪያ ከፍተኛ ፎቅ ህንፃ ላይ የደረሰ ሲሆን አጠቃላይ መግቢያው ወድሟል። የዩክሬን የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ኢጎር ክላይመንኮ እንዳሉት የነፍስ አድን ሰራተኞች ፍርስራሹን እያጸዱ ነው ብለዋል።
ከሟቾቹ መካከል ሦስቱ በአፓርታማው ቦታ ላይ ነበሩ። “አለም አሁንም ሩሲያ ለእኛ፣ ለአሜሪካ እና ለአውሮፓ የሰላም ፍላጎት የሰጠችውን ምላሽ አይቷል። የበለጠ ግልፅ ግድያ ነው” ሲሉ ፕሬዝዳንት ቮሎዲሚር ዘለንስኪ ተናግረዋል። “ያለ ጠንካራ የአፀፋ ምላሽ ሰላምን ማግኘት የማይቻልበት ምክንያት ለዚህ ነው” ሲሉ አክለዋል።
የኪየቭ ስቪያቶሺንስኪ እና ሶሎሚያንስኪ ወረዳዎች በጥቃቱ በጣም የተጎዱ ሲሆን በጥቃቱ አንድ ሰው ሲገደል 20 ሰዎች ቆስለዋል ሲሉ ክሌይመንኮ ተናግረዋል።
