በትግራይ ክልል በሽሬ ከተማ በሚገኙ መጠለያ ጣቢያዎች ውስጥ ከሚገኙ ተፈናቃዮች መካከል በአልሚ ምግብ እጥረት እና በርሃብ ምክንያት የሞቱት ተፈናቃዮች ቁጥር 992 መድረሱን የኢትዮጵያ እንባ ጠባቂ ተቋም የትግራይ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት አስታውቋል።
የቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ ጸሐዬ እምባዬ በ1 ዓመት ጊዜ ውስጥ የደረሰው ሰብአዊ ኪሳራ ተጠንቶ መጠናቀቁን እና ቁጥሩም ከ550 ወደ 992 ከፍ ማለቱን ተናግረዋል።
በአሁኑ ሰዓት በሽሬ ከተማ እና በአካባቢዋ ከ250 ሺሕ በላይ ተፈናቃይ በርሃብና በሽታ እየተሰቃዩ መሆኑን አንስተው፤ የሚመለከተው አካል ትኩረት እንዲሰጣቸው ጥሪ አቅርበዋል።
በሽሬ ከተማ ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ በክልሉ የሚገኙት ተፈናቃዮቹ በ2015 ዓ.ም. ጥር ወር አካባቢ ጀምሮ የሚሰጣቸው ሰብአዊ እርዳታ በመቋረጡ ምክንያት፤ ተፈናቃዮች ለርሃብ እና ለበሽታ መዳረጋቸውን ተናግረዋል።
በክልሉ የዓለም የምግብ ፕሮግራም (WFP) ለእያንዳንዱ ተፈናቃይ 15 ኪ.ግ. ዱቄት እርዳታ እንደሚሰጥ ቢያሳውቅም እየተሰጠ ያለው ግን 9 ኪ.ግ. መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፤ የሚላከው የእርዳታ እህል ከሚያስፈልገው ጋር ልዩነት አለው” ብለዋል።
በአጠቃላይ በትግራይ ክልል ከሱዳን የተመለሱ እና ወደ ቀያቸው ተመልሰው በጸጥታ ችግር ምክንያት IDP በተባለ ተቋም ሥር ያሉትን ሳይጨምር 970 ሺሕ በላይ ተፈናቃዮች በችግር ውስጥ መሆናውን ኃላፊው አስታውቀዋል።
