የጉምሩክ ኮሚሽን በአስመጪዎች እና በጉምሩክ አስተላላፊዎች መካከል የሚደረግ የውክልና ሥርዓት በሕጋዊ መንገድ እንዲመራ አዲስ መመሪያ ማውጣቱን ገለጸ።
ከዛሬ ጥር 28 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ማንኛውም የውክልና ሰነድ በሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ኤጀንሲ በኩል ተረጋግጦ ካልቀረበ በስተቀር በየትኛውም የጉምሩክ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ተቀባይነት እንደማይኖረው ታውቋል።
ኮሚሽኑ ይህንን ውሳኔ ያስተላለፈው፣ እስካሁን ባለው አሠራር ውክልናዎች ሥልጣን ባለው አካል የማይመዘገቡ በመሆናቸው፣ አስመጪዎች በአካል ሳይቀርቡ በሚደረጉ ውክልናዎችና ትክክለኛነታቸው ባልታወቁ የቀረጥ መሰብሰቢያ ቴምብሮች አማካኝነት መጠነኛ የንግድ ማጭበርበር ድርጊቶች ሲፈጸሙ በመገኘታቸው ነው።
ይህም ሕገ-ወጥ ድርጊት የሚፈጽሙ አካላትን ወደ ሕግ ለማቅረብ በሚደረገው ሂደት ላይ እንቅፋት ሲፈጥር መቆየቱ ተገልጿል።
ከዚህ በኋላ የጉምሩክ ሥነ-ሥርዓት ማስፈጸም የሚቻለው በሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ኤጀንሲ በኩል የተረጋገጠ የውክልና ማስረጃ ሲቀርብ ብቻ መሆኑን ኮሚሽኑ አሳስቧል።
ሁሉም የጉምሩክ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶችም ይህንን መመሪያ በጥብቅ ዲሲፕሊን እንዲተገብሩ የታዘዙ ሲሆን፣ የጉምሩክ አስተላላፊዎች ማኅበርም አባላቱ በአዲሱ አሠራር መሠረት እንዲንቀሳቀሱ የማሳወቅ ኃላፊነት ተሰጥቶታል።
ይህ አሠራር የጉምሩክ ሥነ-ሥርዓቱ በእውቀትና በሕጋዊ ማዕቀፍ እንዲመራ እንዲሁም የንግድ ማጭበርበርን ለመከላከል ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ታምኖበታል።
