በአሁኑ ወቅት የካንሰር መድኃኒቶች በሀገር ውስጥ የማይመረቱ ሲሆን አሁን ላይ በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የካንሰር መድኃኒቶችን እና ክትባቶችን በሀገር ውስጥ ለማምረት ሰፊ እንቅስቃሴ እየተደረገ ስለመሆኑ ተነግሯል።
በአርማወር ሀንሰን የምርምር ኢንሲቲትዩት የፋርማሲዩቲካል ኢንድስትሪ ልማት ዘርፍ ም/ዳይሬክተር ረ/ፕሮፌሰር መሳይ ወ/ማርያም የካንሰር መድኃኒቶች እና የክትባት አቅርቦት በሀገር ውስጥ ምርት ለመተካት በቂሊንጦ የኢንዱስትሪ ፓርክ ትልልቅ ፕሮጀክቶች እየተተገበሩ መሆኑን ገልጸዋል።
ምክትል ዳይሬክተሩ አክለውም ኢትዮጵያ ከ72 ዓመታት በፊት በፓስተር ኢንስቲትዩት አማካኝነት እስከ ስድስት የሚደርሱ ክትባቶችን በሀገር ውስጥ ታመርት እንደነበር አስታውሰው፣ ይህ ሂደት ተቋርጦ መቆየቱን ገልጸዋል።
አሁን ላይ “ኢትዮ ባዮ ፋርማ” በተባለ ግዙፍ የመንግስት ፕሮጀክት አማካኝነት ሀገሪቱ የሚያስፈልጓትን ክትባቶች በሀገር ውስጥ ለማምረት የሚያስችል ሰፊ ስራ በቂሊንጦ ፓርክ ውስጥ እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል።
