በየዓመቱ በበሽታው ይጠቃሉ ተብሎ ከሚገመተው ሰው 30ሺ የሚያህሉይ የቲቢ ህመምተኞች ወደ ህክምና ተቋም ሳይመጡ በየቤታቸው እንደሚቆዩ የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።በኢትዮጵያ በየዓመቱ በቲቢ በሽታ ይያዛሉ ተብሎ ከሚገመተው 188ሺ ሰዎች መካከል ተመርምረው ህክምና እየወሰዱ የሚገኙት 150 ሺህ ብቻ መሆናቸውን የጤና ሚኒስቴር የቲቢ ፣ ስጋ ደዌ እና ሌሎች የሳንባ በሽታዎች መከላከልና መቆጣጠር ዴስክ ኃላፊ የሆኑት አቶ ታየ ለታ ተናግረዋል ።
ቲቢ ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍል የሚያጠቃ ተላላፊ በሽታ ይሁን እንጂ በአመዛኙ የሚጠቁት ከ15 እስከ 54 ዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሰዎች ናቸው።በተጨማሪም ዕድሜያቸው ከ5 ዓመት በታች የሆኑ ሕፃናት፣ የምግብ እጥረት ያለባቸው፣ ቲቢ እንዳለባቸው ከተረጋገጠ ሕሙማን ጋር አብረው የሚኖሩ እንዲሁም በተጨናነቁና በተፋፈጉ ቦታዎች የሚገኙ ሰዎች ለበሽታው ይበልጥ ተጋላጭ እንደሆኑ ተጠቁሟል ።
የቲቢ በሽታ 80 በመቶ የሚሆነውን የሚያጠቃው ሳንባን ሲሆን ምልክቱ ሁለት ሳምንትና ከዚያ በላይ ለሆነ ጊዜ የቆየ ሳል በተለይም ሳሉ አክታ ያለውና ደም የቀላቀለ ነው ተብሏል ። በተጨማሪ በደረት አካባቢ የውጋት ስሜት ተጠቃሽ መሆኑንም አቶ ታዬ ጨምረው ተናግረዋል። ቲቢ በአግባቡ ከታከመ የሚድን በሽታ ሲሆን መድኃኒት በታዘዘው መጠንና ጊዜ ባይወሰድ ግን አስቸጋሪ በመሆኑ ሕመምተኛው የታዘዘለትን መድኃኒት ሳያቋርጥ በየቀኑ መውሰድ ይጠበቅበታል።
ሕክምናው ከተቋረጠ ግን የበሽታ መንስኤ የሆነው ባክቴሪያ የፀረ-ቲቢን መድኃኒቶችን በመላመድ በመደበኛው የቲቢ ሕክምና መዳን የማይችል የቲቢ ዓይነት እንዲፈጠር ያደርጋል። ቲቢ የሚተላለፈው በአብዛኛው በትንፋሽ አማካኝነት መሆኑንና አንድ በሳንባ ቲቢ የተያዘ ሕመምተኛ በሚስልበት፣ በሚያስነጥስበት፣ በሚናገርበት ወቅት የቲቢ በሽታ አምጪ ባክቴሪያን የያዙ የአክታ ብናኞች ወደ አየር ይረጫሉ። በዚህም በአቅራቢያው ያሉ ሰዎች አየር ወደ ውስጥ በሚተነፍሱበት ጊዜ በቀላሉ ወደ ሳንባው ውስጥ ገብተው ለማጥቃት ዕድል እንደሚያገኙ ተጠቁሟል ።ኢትዮጵያ በአለም ላይ የቲቢ በሽታ ጫና ካለባቸው 30 ሀገራት ውስጥ አንዷ ናት። 19ኛው አለም አቀፍ የቲቢ በሽታ ቀን እየታሰበ ይገኛል ይህ አለም አቀፍ የቲቢ በሽታ ቀን ቫይረሱ የተገኘበት ቀን በማሰብ የማስተማር እና ግንዛቤ የመፍጠር ስሬ የሚሰራበት ቀን ነው።
@ብሥራት ሬዲዮ
