በ2017 ዓመት ከተሰሩ በርካታ ጥናቶች ዉስጥ 30 የሚሆኑት በዓለም አቀፍ ታዋቂ የምርምር ህትመቶች ላይ መታተማቸዉ ተገልጿል ። እነዚህ ጥናቶች ላለፉት አራት ዓመታት ሲጠኑ እንደነበር እንዲሁም ዉጤታቸዉ በቅርቡ ለህብረተሰቡ ይፋ እንደሚሆኑ የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት አስታዉቋል።
በኢትዮጵያ የጥቃቅን ንጥረነገሮች እጥረት በሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች ላይ በከፍተኛ ሁኔታ መኖራቸዉን ጥናቶች እንደሚያሳዩ የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የስርዓተ ምግብና የአከባቢ ጤናና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶክተር ማስረሻ ተሰማ ለብስራት ሬዲዮ ተናግረዋል ።
የፎሊክ አሲድ እጥረት የነርቭ ዘንግ ክፍተት ችግርን የሚያመጣ ሲሆን በተለይም ነፍሰጡር እናቶች ከእርግዝና በፊት በቂ የሆነ ፎሊክ አሲድ በሰዉነታቸዉ ከሌለ የሚወለዱ ልጆች ለዚህ ችግር ተጋላጭ እንደሚሆኑ ተገልጿል ። በዚህም ከአፍሪካ ሀገራት ኢትዮጵያ ከፍተኛዉን ቁጥር ትይዛለች ።
ለዚህም መፍትሄ የሚሆነዉ ጨዉ ዉስጥ የፎሊክ አሲድን በመጨመር ማበልፀግ ሲሆን ለመጀመሪያ ጊዜ በዓለም ደረጃ ጥናቱ የተጠናቀቀ ሲሆን ዉጤታማነቱ በቅርቡ ይፋ ይሆናል ሲሉ ዳይሬክተሩ ተናግረዋል ። የዛሬ 10 እና 20 ዓመት ገደማ በእንቅርት የሚጠቁ ሰዎችን ማየት የተለመደ የነበረ ሲሆን አዮዲን ጨዉ ዉስጥ በመግባቱ ይህን ቸግር መቅረፍ ተችሏል።
የፎሊክ አሲድ እጥረት በክልሎች የበርካታ ህብረተሰብ የጤና ችግር መሆኑን የገለፁት ዶክተር ማስረሻ ጤናማ ያልሆኑ አመጋገቦች ላይ በፖሊሲ ደረጃ ህጎች እንዲወጡ የሚያግዙ በርካታ ጥናቶች መጠናታቸዉ ይህም ከኢትዮጵያ አልፎ ለአለም ህብረተሰብ እና ለአፍሪካ ሀገራትም ጥቅም ይኖረዋል ብለዋል ።
