ልጆች ረጅም ሰዓት በስልክና በቪዲዮ ጌሞች ላይ ማሳለፋቸው፣ መናገር የሚችሉ ሆነው ከተወለዱ በኋላ አንደበታቸው እንዲያዝ እያደረገ መምጣቱ ተገልጿል።
ይህም በተፈጥሮ ከሚመጣ ኦቲዝም ባልተናነሰ ለዲጂታል ኦቲዝም እያጋለጣቸው መሆኑን ፍቅር ኢትዮጵያ የአዕምሮ እድገት ውስንነት ብሔራዊ ማህበር ስራ አስፈፃሚ ወ/ሮ ሸዋጌጥ ክብረት ገልፀዋል።
በአሁኑ ወቅት ወላጆች ልጆቻቸው ሲያለቅሱ ወይም ሲያስቸግሩ ስልካቸውን ሰጥተው ዝም ማሰኘትን እንደ ዋነኛ አማራጭ መውሰዳቸው በትውልዱ ላይ ትልቅ አደጋ እየጋረጠ ይገኛልም ብለዋል።
ዲጂታል ኦቲዝም የሚባለው ስያሜ ልጆች ከስክሪን ጋር ረጅም ጊዜ በማጥፋታቸው ሳቢያ የሚፈጠር የተግባቦትና የማህበራዊ ግንኙነት ክፍተት መሆኑን ያስረዱት ወ/ሮ ሸዋጌጥ፥ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሀገሪቷ ላይ እየተስተዋለ የመጣው የህፃናት ስልክ አጠቃቀም ጤነኛ ሆነው የተወለዱ ህፃናትን ሳይቀር መናገር አቅቷቸው ወደ ማህበራቸው እንዲመጡ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
ስራ አስኪያጇ ልጆች ዝም ብለው ስልክ ላይ ጊዜ ካጠፉ አያወሩም፤ ቃላት ማውጣት ያለበት ላንቃቸውም ዝም እያለ ነው የሚሄደው ያሉ ሲሆን ፣ በሕክምና ሲረጋገጥም “ዲጂታል ኦቲዝም” ሆኖባቸው የተገኙ የብዙ ህፃናት ቁጥር በአዲስ አበባም ሆነ በክልል ከተሞች በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መሆኑን ገልጸዋል።
ይህንን ችግር ለመቅረፍም ትልቁ ሥራ ወላጆች ላይ እንደሚጣልና በተለይም ህፃናት ትምህርት ቤት ከመግባታቸው በፊት ባለው ከ1 እስከ 4 ዓመት ባለው የዕድሜ ክልል ላይ ከፍተኛ ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ አሳስበዋል።
